የአብስራ

Description
እምነት ~ ተስፋ ~ ፍቅር
FAITH HOPE LOVE
الإيمان أمل الحب ~ 🤎

📬 @yeabsra_tsega

በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@Yeabsira_Tsega
We recommend to visit

ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ

Last updated 2 months, 3 weeks ago

Last updated 2 months, 2 weeks ago

ይህ ስለ Manchester United መረጃዎችን የሚያገኙበት የ Telegram ቻናል ነው 🇪🇹
--------------------------------------------------------------
☞︎| ስለ ማንቸስተር ዩናይትድ ትኩስ መረጃዎች
☞| ቀጥታ ስርጭቶች ከየስታድየሞቹ
☞| የዝውውር ዜናዎች
☞| ስለ ማንችስተር ዩናይትድ ታሪኮች

📩 ለማስታወቂያ ስራ DM :- @Marcoabdu

Last updated 1 month, 2 weeks ago

1 month ago

<<እስከዳር>>
ክፍል ፲፰

እስከዳር ከኮሌጅ ስትገባ አባቷ ሶፋ ላይ ተቀምጦ ተገጣጠሙ።

“የት ነበርሽ?”

ዝም ብላው ወደክፍሏ መንገድ ቀጠለች።

“እስከዳር...”

“አቤት...”

“የት ነበርሽ እያልኩሽ ነውኮ...”

“ይሄን ለማወቅ ዛሬ መጠየቅ ሊጠበቅብህ አይገባም ነበር...”

“እንዴት እንዴት ነው የምትመልሺልኝ?”

“ደክሞኛል ልግባና ልረፍ...”

“የት ቆይተሽ ነው?”

“ኮሌጅ ነበርኳ የት እሆናለሁ በትምህርት ቀኔ...”

“ምሳ በልተሻል?”

መልስ ሳትሰጠው ገብታ ክፍሏን ከውስጥ ቆለፈችው።

ጌታቸው አቀርቅሮ ተቀመጠና ጥቂት ቆይቶ በዝግታ ቀና ብሎ ጥግ ላይ የተቀመጠውን የሟች ሚስቱን የርስትን ፎቶ ተመለከተ።

~ ~ ~

የህንፃ ግራውንድ ውስጥ ባለ ሰወር ያለ ክፍል ውስጥ...

“አቡሻ...”

“ኧኸ...”

“እና ምን አልከኝ?”

“አይ በቃ ልጆቹ ከእኔ ብዙ ሩቅ አይደሉም ከዛ ሰውጋ ደግመው እንዳይሰሩ ነግሬያቸዋለሁ...”

“ስራ አልከው? የምር ከባድ ነውኮ”

“አይ ቆሴ አንቺ መች ይገባሻል ዘመኑ ከፍቷል...”

“እኛው ነንኮ ያከፋነው... እሺ ታዲያ ለእነሱ ትዕዛዙን የሰጣቸውን ሰው ልታሳውቀኝ አትችልም?”

“እ ምን አለህ መሰለህ ማርቆስ... የምር እኔ አንተ እንደቤተሰብ ስለሆንክ ልንገርህ እንዲህ ባሉ ጉዳዮች ከማንምጋ ባትነካካ መልካም ነው...”

“አቡሻ እንድትመክረኝ አይደለም የመጣሁት እና ደሞ መነካካት አትበለው ተደርሶብን እንጂ ማንም ላይ ደርሰን አይደለም... እንዴ አንተ ወንድምህ እንደዛ ያለምክንያት ቢደበደብ ዝም ብለህ ትቀመጣለህ?”

“እሺ ቢያንስ ላማክር በምን አይነት መንገድ ነው ልትሄድ ያሰብከው?...”

“ወዴት?”

“ሃሃ ሃ ማለቴ በህግ ነው ወይስ በራስህ?”

~             ~             ~

“የእኔ እህት ልትዪኝ የፈለግሽውን በቀጥታ ለምን አትነግሪኝም? ይቅርታ አድርጊልኝ ዙሪያ ጥምጥም ሆነብኝ ወሬሽ...”

“አብረን እንስራ?”

“ማለት ምን?”

“የነገርኩህ ህገወጥ ስራዎችና በሌላ መልኩ ደሞ ስነምግባር አልባ ድርጊቶች ሁሉ የአንድ ሰው ናቸው... እርሱም ሰው የቀድሞ የእስከዳር ፍቅረኛ ነው። እሷ እንኳ ጨርሳ አላወቀችውም... እዚህ ከተማ ላይ እንደልቡ የሚፈነጭበት ጊዜ እንዲያበቃ አግዘኝ!...”

እዩኤል በግራ መጋባት የሚለው ጠፍቶት ዝም ብሎ ወደመንገዱ ያይ ጀመር።

“ወደሰፈርህ ልሸኝህ... አሁን ስለደከመህም እስከአመሻሽ አስበህበት ንገረኝ አላስጨንቅህም... ግን እመነኝ ለአንተም ለእስከዳርም ከዛም በላይ ለብዙዎች የሚተርፍ ትክክለኛ ውሳኔህ ይሆናል!”

መኪናዋን አስነስታ...

“ልሸኝህ ወዴት ነህ?”

~             ~             ~

“ምን ሳስብ ነበረ መሰሎት ዛሬ?”

“ስለእዩኤል ነው ሌላ ምን ታስቢያለሽ ባለቤቴ... መቼም ስለእኔ አይሆን...”

“ለነገር አይቸኩሉ...”

“እሺ ምን ስታስቢ ዋልሽ?”

“ያኛውን ክፍል ለበዓልም እንዲሆን ቀደም አርገን ለምን ቀለም አናስቀባውም...”

“የትኛው ነው ያኛው ክፍል?”

“ያኛው ነዋ የተቆለፈው...”

“የእዩኤል ክፍል አይደል እንዴ እሱ?”

“እኮ ከፍተን ቀለም እናስቀባለት... ሲመጣ ደስ ይለዋል... እዚህ እያለ ጊዜ ቢያገኝና ቢችል ቀለም ቢቀባው ደስ እንደሚለው ሲያወራኝ ነበር...”

“እና ስለእዩኤል አላሰብኩም ነው የምትዪኝ?”

አሉና በነገሩ ሳቁ የእዩኤል አባት...

“ጥሩ ቀለም ቀቢ አናግሬያለሁ... ሲመጣ ይከታተሉትና ሂሳቡን ከፍለው ይሸኙት ነግሬያለሁ...”

ብለው የእዩኤል እናት ወደጓዳ ገቡ...

“የእኛስ መኝታ ክፍል ቀለም አይቀባም?... ወቸ ጉድ...”

~             ~             ~

እስከዳር ምግብ ሰርታ ቋጠረችና ከቤቷ ወጥታ ደስ እያላት ወደእዩኤል ቤት ለመሄድ መንገድ ጀመረች።

በትራንስፖርት ላይ ሆና በታክሲው መስኮት የምታልፍበትን መንገድ ትቃኛለች።

እየጠለቀች ያለችው ፀሃይ ፊቷ ላይ ስታርፍ ፈገግ ትሰኛለች።

~             ~             ~

“በቃ በዚህጋ እገባለሁ”

አለ እዩኤል የመኪናውን ቀበቶ እየፈታ...

ሊሊ መኪናዋን አቆመች።

“እ... ለበጎ ሃሳብ መዘግየት አልፈልግም...”

“ምን እያልከኝ ነው?”

“ውስጤም እየነገረኝ ነው አምኜሻለሁ...”

“ስለዚህ?”

“በቃ አንድ ላይ ማድረግ ያለብንን እናደርጋለን...”

“ደስ ብሎኛል አመሰግናለሁ እሺ በጣም...”

ሊሊ በደስታ ከተቀመጠችበት ተንጠራርታ ልታቅፈው አለችና አፍራ መለስ ብላ አጎንብሳ አመሰገነችው።

ተሰናብቷት ወረደ።

~             ~             ~

እስከዳር ከአስፓልቱ ማዶ የቋጠረችውን ምግብ እንደያዘች ደንዝዛ ቆማ ቀረች።

እዩኤል ከአንዲት የቤት መኪና ሲወርድ ተመልክታ ሳትጨርስ የመኪናውን መሪ የጨበጠችው ሊሊ መሆኗን ስትመለከት ማመን ተሳናት።

የምትለው ጠፍቷት ደርቃ ቀረች።

ሊሊ መኪና ርቃ ሄደች።

እዩኤል ወደቅያሱ ገብቶ ከእይታ ተሰወረ።

እስከዳር ልቧ እየደከመ እንባዋ አንዴ ወረደ።

~             ~             ~

ይቀጥላል...

(ጥቂት ቀረን... ስለመከታተልዎ ላቅ ያለ ደስታ ይሰማኛል... ማበረታታት ከወደዱ በ “የአብስራ” ዩቲዩብ ቻናልም ቤተሰብ ይሆኑ ዘንድ በአክብሮት ተጋብዘዋል🖤)

✍🏾 በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

1 month ago

<<እስከዳር>>
ክፍል ፲፯

በጀርባው እንደተኛ አይኖቹ ጣራው ላይ ተተክለዋል...

“ምንድነው የሆንከው ውዴ?”

“ምን ሆንኩ?”

“እንቅልፍ አጥተሃልኮ...”

“ተኚ አሁን ነው የነቃሁት...”

“ኧረ ዝም በል ባክህ ልጁን ላጠባ ተነስቼ ሳይህ አልተኛህም... ልጁ ከተኛ ስንት ሰአቱ አንተ ይኸው እንቅልፍ አልወሰደህም...”

“እንቅልፍሽ አልመጣ ሲልሽ እየተደበርሽብኝ ነዋ?... ተኚ ለራስሽ ቀን ስራ በዝቶብሽ ነው የምትውዪው...”

“አንተስ?”

“ተኚ እተኛለሁ...”

“አንተ ቀን ስራ ላይ አይደል ያሳለፍከው?”

“ምንድነው ውዴ ምትጨቃጨቂኝ ተኚ...”

“እውነቱን ንገሪኝ ካልክ እንቅልፍ ማጣትህ ብቻ ሳይሆን ሰሞኑን ባህሪይህ ራሱ በጣም ተቀያይሯል የሆንከው ነገር ካለ ሚስትህ አይደለሁ ንገረኝ?...”

“በዚህ ሌሊት አንነታርክ ህፃኑም ተኝቷል አንረብሸው ተኚ...”

ዞሮ ጀርባ ሰጥቷት ተኛ።

~ ~ ~

መጠነኛ ካፌ ውስጥ...

“ተገናኘንኮ...”

“ከማንጋ?”

“ከእስኪዬ ጋር ነዋ...”

“ኧረ?... እደበቃታለሁ ትንሽ ጊዜ አላልከኝም ነበር?”

“አልቻልኩማ በናትህ... አሳዘነችኝ ባላጠፋች ለምን ትቀጣ በዛ ላይ እሷ ሚስኪን ናት ባላገኛት ችግሮቹን ሁሉ በእሷ ምክንያት እንደመጡ አድርጋ ነው የምትቆጥራቸው።”

“ምን አለች ግን ስታይህ?”

“የእኔ ሚስኪን ባየሃት ልክ ልጅ እያለሁ ትምህርት ቤት በጨዋታ መሃል ወድቄ የሆነ ቁስል ይዤ ቤት ስገባ እናቴ እንደምትሆነው ነው የሆነችው... ገረመችኝ ሃኪም ቤት እንሂድ ስትለኝ... ደሞ ከፋት የምር ረጅም ሰአት ዝም ብላ እያየችኝ ነበር...”

የማርቆስ ስልክ ጠራ...

“ሄሎ...”

“አንተ ኧረ ኬዙ ከባድ ነው...”

“ምን አልከኝ ሄሎ...”

ሆነ ብሎ የስልክ ልውውጡን ከእዩኤል ለማራቅ ኔቶርክ እንደሚፈልግ ሰው ብድግ ብሎ ራቀ።

~             ~             ~

እስከዳር ትራስ ታቅፋ በተቀመጠችበት ያለፈ ታሪክ ማስታወስ ጀመረች።

*“አንቺን የሰጠኝ ፈጣሪ ሃላፊነት ጥሎብኛል...”

“ምን አይነት?”

“ልክ ንጉስ ግዛቱን የሚያስጠብቅበት አይነት...”

“እኔ ንግስት አይደለሁም?”

“እሺ ልክ ንጉስ ንግስቲቱን የማያስነካበት አይነት...”

“እንጋባ የምልህ ለዚህ ነውኮ ካላገባኸኝማ የአንተ ስለመሆኔ መተማመኛ የለህም... ንግስት እንጂ ንግስትህ አይደለሁም...”

አለች ፈገግ እያለች...

“እስቲ አላገባሃትምና እድሌን ልሞክር ብሎ አንዱ ይድረስብሽና ያኔ የማን ንግስት እንደሆንሽ ታያለሽ...”*

በፍጥነት ስልኳን አንስታ ደወለች።

ይጠራል አይነሳም...

ደግማ ደወለች።

“የእኔ ውድ ንግስት”

“አንተ ውሻ አንተ ነህ አይደል? ያንተ ስራ ነው አይደል?”

ስልኩን ጆሮዋ ላይ ዘጋው።

የታቀፈችውን ትራስ ወደጎን ትታ ተነሳችና ድግማ ደወለች።

“ይቅርታ አድርጊልኝና ስድድብ አልፈልግም...”

“ማን እንደሆንክ ነው የምታስበው?”

“ምን ጉድ ነው? ምን ሆነሽብኝ ነው የእኔ እስከዳር?... እንገናኝ ራት ልጋብዝሽ ይቅርታ አድርጊልኝ ስላልኩሽ ብቻ ነው እንዲህ ድንገት ደውለሽ የምታቃልዪኝ...”

“ሴሰኛ ብቻ ነበር የመሰልከኝ ወንድ አይደለህም እሺ አንተ ሰውም አይደለህም!”

የምትለው ግራ ስለገባት እንባዋ ቀደማት።

“በኋላ የሚፀፀትሽን ነገር አትናገሪኝ እኔ ይቅርታ ል....”

አውርቶ ሳይጨርስ በንዴት ስልኩን ዘጋችበት።

~             ~             ~

እዩኤል ከመስሪያ ቤት ወጥቶ ወደዋናው አስፓልት ሲያመራ አንድ ጥግ ይዞ የቆመ መኪና ተከተለው።

ደረሰበት።

ሴት ናት የመኪናውን መስታወት ዝቅ አድርጋ...

“ወንድሜ...”

እዩኤል በግራ መጋባት ጎኑ ወዳለው መኪና ዘወር ብሎ

“እኔን ነው?”

“አዎ ላወራህ ፈልጌ ነው...”

ተረጋግቶ ቆሞ ጥቂት አሰበና...

“ስልክ የደወልሽልኝ ሴት ነሽ አይደል?”

“አዎ እሺ በለኝና ወደመኪናው ገብተህ ላናግርህ...”

እንደማይፈራ ለማሳየት በንዴት ወደመኪናው ገባ።

“ደግሜ ልንገርሽ እኔ እስከዳርን አፈቅራታለሁ እና ማን እየላካችሁ እንደሆነ ባላውቅም እኔ ማናችሁንም ፊት ለፊት ለማግኘት እንደማልፈራና አምኜበት ከምኖረው ህይወት ወደኋላ እንደማልል እወቁ!...”

ሊሊ በሃዘን እያየችው...

“ታድላ እስከዳር... የእውነት ትክክለኛውን ሰው አግኝታለች በህይወቷ...”

“ማነሽ አይቺ የእኔ እህት?”

“አታውቀኝም እስከዳር ለማንም ስለእኔ አላወራችም... ግን ብታወራ እንኳ እኔ ማለት እስከዳርም ያወቀቻትን አይነት ሴት አይደለሁም...”

~             ~             ~

ማርቆስ በእርጋታ ወደአንድ ሰፊ የመንደር ፑል ቤት ውስጥ ገባ።

“ቆሴ መጣ...”

“እኔ አላምንም አንቺ እሳት ቆሴ ነሻ... እንኳን ደህና መጣሽ ወዳደግሽበት ቤት...”

“ያራድዬ ልጅ ስራ ስትይዢ ላሽ አልሺን ብዬ ነበር...”

“እሱ ማለት በዩኒፎርም ከትምህርት ጎን ለጎን እዚህ ከቻሳ እያለ ያበደ ሽቀላ ይሰራ የነበር የፑሉ ጠበብት ማርቆስ ነው...”

“በሉ በሉ አትሰካክሱኝ...”

“ስላገኘሁህ ደስ ብሎኛል ስላንተ ዝና ሰምቻለሁ...”

አለ አንድ ካሉት አነስ ያለ ወጣት ልጅ...

“የምር እንኳን ጎራ አልክ እኔኮ ማናገርም ሸመመኝ ከግቢ ስትመለስ ሌላ ሰው ስትሆንብን እኛም እንደሙድህ ብለን ፈታን...”

“ሰፈርም ትንሽ ራቅ ስላልኩ ነው እናንተንማ እንዴት ችላ እላለሁ... አቡሻ የለም እንዴ?”

“አቡሻ... እስቲ ግራውንድ ውረጂና እዪያት...”

“ይመቻችሁ... በሉ እሺ...”

አልፏቸው ሌሎች ቁማርተኞችንም አልፎ ወደታች ወረደ።

ከአንድ ባለባርኔጣ ሰውዬጋ ተላለፈ።

~             ~             ~

ይቀጥላል...

(ስለመከታተልዎ ላቅ ያለ ደስታ ይሰማኛል... ማበረታታት ከወደዱ በ “የአብስራ” ዩቲዩብ ቻናልም ቤተሰብ ይሆኑ ዘንድ በአክብሮት ተጋብዘዋል🖤)

✍🏾 በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

1 month ago

<<እስከዳር>>
ክፍል ፲፮

እዩኤል ከማን እንደሆነ ያላወቀውን የስልክ ጥሪ አነሳ...

“ሄሎ ማን ልበል?”

“አታውቀኝም...”

“እኮ ማን ልበል አልኩኮ ምንድነው ችግር አለ?”

“የለም...”

እዩኤል ጥርሱን ነክሶ ከሶፋው ተነስቶ ቤቱ ውስጥ ግራ ቀኝ ይመላለስ ጀመር።

“የደወልኩልህ ከቻልክ በአካል ላገኝህ ስለፈለኩ ነው...”

“ይቅርታ የእኔ እህት አልገባኝም ታውቂኛለሽ?...”

“እዩኤል ነህ አይደል?”

“አዎ...”

“ለብርቱ ጉዳይ ላገኝ ፈልጌ ነው...”

“ማን ነሽ?”

“ሜሮን እባላለሁ... እመነኝ ምንም መጥፎ አላማ የለኝም... በቀን አንተ በመረጥከው ቦታ እንገናኝ...”

“ምንድነው ከእኔ የምትፈልጉት?... ከጀርባሽ ያለው ማንም ቢሆን ንገሪልኝ ጨዋ ብቻ ሳልሆን ምንም የማልፈራ ወንድ ነኝ እሺ!...”

ስልኩን በብሽቀት ዘጋው።

ሊሊ ስልኩን ጆሮዋ ላይ ስለዘጋባት በረጅሙ ተንፍሳ ዝም አለች።

~ ~ ~

ጨለም ያለው ቤት ውስጥ... የአልኮል መጠጥ በሁለት ሰዎች መሃከል አለ።

“እንዴት ነበር ቆይታችሁ?”

“ጥሩ ነበር...”

“ሂድ ከዚህ... የወሬ ጥሜን አትቁረጥብኝ ዘርዘር አርገህ ንገረኝ እንጂ... እንዴት ነበር እንጂ ምን ነበር አላልኩህም'ኮ?”

“እንዳልከን አስጠንቅቀነዋል... ግን በመጀመሪያው ቡጢ ብቻ ስላልተረጋጋ አብረውኝ ከነበሩት አንደኛው ሌላ ጠንከር ያለ ቡጢ ደግሞት ደንግጬ ነበር...”

“ሃሃ ሃ ሃ አንተም አልተረጋጋህም ነበር እንዴ?”

“አይ ሳይሆን ያልከን አንድ ደህና ቡጢና አንድ መልዕክት አልነበር?”

“እሱ ፀባዩ ታይቶ ማሻሻያ እንደሚደረግበት ነግሬሃለሁኮ...”

“በቃ ልሂድ በጣም ጨልሟል እቤት ይጠብቁኛል...”

“በስራ ትንሽ ቢዚ ሆኜ ነው ወዲያው ‛ቼክ’ ያላደረኩህ... አሁን ፋታ ሳገኝ ነው ልጠራህ የተገደድኩት በል ሂድ...”

ከሳሎን ወደደጅ አመራ...

ጥበቃው በሩን ከፍቶ አስወጣው።

ሲወጣ ሊሊ ከኪችን ሆና ተመለከተችው...

~             ~             ~

የእዩኤል ቤተሰብ ቤት ቡና ተፈልቷል።

“ተመስገን በዪ እስቲ ተመስገንም ልመጂ...”

“አልኩኮ ጌታው...”

“አይ የእዩኤል እናት... ደወለ ደህና ነኝ አለ አንቺ ግን አሁንም ፊትሽ ጨርሶ አልፈታም...”

“አይ እንግዲህ አርፈው ቡናዎን ይጠጡ...”

“ነግሬሽ ነበር ደህና ነው ብዬ... የእኔ ልጅኮ በአባቱ ነው የወጣው ጀግና ነው ምንም አይሆን...”

“በእርሶ ቢወጣስ እኔ ደስ ይለኛል እንጂ አልቀና...”

የቤት ስራ አጋዣቸው ልጅ ፈገግ አለች።

~             ~             ~

“ሄሎ እዩዬ”

“አቤት እስኪዬ?”

“ምን አድርጌህ ነው?”

“ምን መቼ ፍቅር...”

“እና ስልክህን አላነሳ ስትለኝኮ ተጨነኩ ከዛ የምር ቤት ልመጣ ስል አልተመቸህ ይሆናል ብዬ ስላሰብኩ ሃሳቤን ቀይሬ እቤት ቁጭ አልኩ...”

“የእኔ አበባ ኧረ ምን ባይመቸኝ ታዲያ አንቺን እርቃለሁ እንዴ?”

“እሺ አልናፈኩህም?”

“ናፍቀሽኛል ለዛ አይደል የደወልኩልሽ...”

ኩርፊያዋ በድምጿ እያስታወቀ

“እና በስልክ አውርተን በቃ?”

አለች...

“አይ እንገናኛለን...”

ጥቂት ዝምታ...

“የት ሄድሽብኝ ሄሎ እስኪዬ...”

“እዩ...”

ኩርፊያዋ በእንባ መተካት ተጀመረ።

“ሰለቸሁህ እንዴ?”

“ኧረ በስማም ምን ሆነሻል...”

“ሰለቸውሃ?... እና ደሞ ትንሽ ስታውቀኝ ከበድኩ እንዴ? ከእኔጋ መሆን ይከብዳላ?... እና እና እና ሌላ ጊዜ በየቀኑ እንገናኝ የምትለኝ ልጅ ሁለት ቀን ሆነህ'ኮ ዝም ካልከኝ...”

“ልዋሽሽ ስላልፈለኩ ነው እግዚአብሔርን የእኔ ፍቅር...”

“ምን ምንድነው የምታወራው...”

“አሁን እንገናኝ?”

“የት?”

“እመጣለሁ ቤትሽ... ይዤሽ እወጣለሁ እ ይኸው መጣሁ...”

እንባዋን እየጠረገች...

“እየጠበኩህ ነው...”

~             ~             ~

አንድ ድርጅት ውስጥ

“እሺ እንዴት ነው ስራ?”

“አሪፍ ነው አለቃ...”

“በርቱ...”

“እሺ አለቃ...”

“ደሞ እነግርሃለሁ ብዬ...”

“ምን?”

“ቢሮ ውስጥ ለምንድነው ይሄን የውጪ ፊልም አክተር የሚያስመስልህን ባርኔጣ የምታደርገው?...”

“ያው ዝም ብዬ ነው... እወደዋለሁ”

አለ ሳቅ ሊል እየሞከረ...

“ተው ተው ይሄኮ መድረክ አይደለም የስራ ቦታ ነው በል አውልቀውና ስራህ ላይ ትኩረት አድርግ... ያምርብሃል ግን ይሄ እንደምታውቀው የስራ ቦታ...”

“ይገባኛል...”

ቅሬታውን በሳቁ እየደበቀ ባርኔጣውን አውልቆ ጠረጴዛው ላይ አስቀመጠው።

“አንተ እኔ ዞር ስል ልታደርገው ነው...”

ብድግ አደረገበት...

“በል በል በኋላ ከስራ ስትወጣ ናና ቢሮ ተቀበለኝ በክብር አስቀምጥልሃለሁ... ሃሃ ሃ”

ሄደ።

መላጣ ጭንቅላቱን ዳሰሰ።

~             ~             ~

እስከዳር ከቤቷ ስትወጣ ጥቁር መነፅር አድርጎ የሚጠብቃትን ፍቅረኛዋን አየችው።

በሩን እንደዘጋች ሮጣ ተጠመጠመችበት...

ከእቅፉ ወጥታ ቀና ብላ ፊቱን ስታየው አይኑ ስር አብጦ በልዟል። እጇ እየተንቀጠቀጠ ፊቱን ዳሰሰችው።

“እዩዬ?”

~             ~             ~

ይቀጥላል...

(ስለመከታተልዎ ላቅ ያለ ደስታ ይሰማኛል... ማበረታታት ከወደዱ በ “የአብስራ” ዩቲዩብ ቻናልም ቤተሰብ ይሆኑ ዘንድ በአክብሮት ተጋብዘዋል🖤)

✍🏾 በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

3 months, 3 weeks ago

“...ላለማንከስ + ለመመለስ...”

ወንድማችሁ የአብስራ ነኝ...

በዚህች ምድር ስንኖር ሁላችንም የራሳችን ፈተናዎች አሉብን...
የህይወት ጥያቄና ሸክም ፈተናና ችግሮች እንዳሉ ሆነው እኛ ለሁኔታዎች የምንሰጠውም ምላሽ አለ።

እስካሁን የእግዚአብሔር ምህረት በዝቶልኝ በኖርኩበት እድሜ ያሳለፍኩትም ያለፍኩበትም ብዙ እንደሆነ አስባለሁ። ራሴንና ኑሮዬን ስቃኝም የማልክዳቸው ጉዳዮች አሉኝ በበጎም ሆነ በጉድፍነትና በምሰሶነት የምጠቅሳቸው...

ትልቅ ነገር የመስራት፤ በጎ ተፅዕኖ የመፍጠርና ለተፈጠርኩበት መልካም አላማ የመኖር መሻቴና የሰራኝም እግዚአብሔር የሰጠኝ መክሊት ቀላል የማይባል ሆኖ ሳለ በስጋ በዚህች አለም ስመላለስ የደከምኩበት የወደቅሁበት እንዲሁም ተስፋ ሁሉ ያስቆረጠኝ ታሪክም አለኝ...

በምከተለው እምነት እኔ የ“እግዚአብሔር ቤተመቅደስ” ስለመሆኔ የማምን ሳለሁም በ Pornography(የወሲብ ፊልም) እና Masturbation(ራስን በራስ የማርካት) ሱስ ውስጥ በመገኘት ደግሞ በተደጋጋሚ ሃጥያት በቅድስና እንድኖርለት የሚፈልገውን ከሞት ያዳነኝን አምላኬን ብዙ በድያለሁኝ...

በትምህርት በስራና በህልም ደረጃ የሚጠበቅብኝን ያህል አለመትጋቴን ከሁሉ የሚልቅ መንፈሳዊ ህይወቴንም በአምላኬ ፀጋ በታማኝነት አለመያዜን ሳስብ አንካሳነቴ በጉልህና በግልፅ ይታየኛል።

ስለሆነም እግዚአብሔር በህይወቴ ያለውን የመንግስቱንና የፅድቁን ሃሳብ ከትላንቶቼ ይልቅ በሙሉ ልብ እፈልግ ዘንድ እንዲሁም በኑሮዬም ፈቀቅ ስል ለማየት ካለኝም ጉጉት የተነሳ እኔ ደካማና ሃጥያተኛው ወንድም ለተወሰኑ ጊዜያት ከግላዊ ሶሻል ሚዲያዬ ሁሉ ገለል እላለሁ።

ይህን ሁሉ ስፅፍ ድካሜን የሚገልፅልኝ መጣኝ ቃል አገኘሁ በሚል ድፍረት አይደለም ደግሞም ራሴን ብዙ ሰዎች እንደሚከታተሉት የሚዲያ ሰው ቆጥሬም አይደለም ግና እንዲሁ ፅሁፎችና ፖስቶች ሳጋራ ሆነ ብላችሁም ይሁን በአጋጣሚ የምትጋሩኝን ቤተሰቦቼን በማክበር ነው።

እግዚአብሔር ፈቅዶ በምህረቱና በፀጋው ብዛት በጊዜው ወደማህበራዊ ሚዲያ ስመለስ እንደምንገናኝ ተስፋ አደርጋለሁ!... ሁላችሁም ለያላችሁበት ሁኔታ እግዚአብሔር መልካም እንደሆነ ዳግም እያስታወስኩ መልካሙንም እመኝላችኋለሁ... እወዳችኋለሁ?

“...ዳዊት እጅግ ተጨነቀ፤ ዳዊት ግን በአምላኩ በእግዚአብሔር ልቡን አበረታ።”
— 1ኛ ሳሙኤል 30፥6

4 months ago

<<የነልሳን እናት...>>
ክፍል ፲

(የመጨረሻ ክፍል!)

“ምን ሆነህ ነው?”

አለችኝ ኢቫ እንደሌላ ቀን ፊቴ ባይበራ...

“እ?”

"ምነው?”

ምን ልበላት...

እማዬና አባዬን ያስተከዛቸው የነልሳን እናት ነገር... በጊዜው እኔን እንደዛ ለመግረፋቸው ምክንያት የሆኑት ሴት በአካል ቤታችን መምጣታቸው ነበር።

ያኔ ቤት እንደተመለስኩ እማዬ አረጋግታ ነገረችኝ...

“አቢዬ...”

"አቤት...”

"የነልሳንን እናት አገኘሃቸው?”

“አይ...” አኩርፌ የአልጋዋ ጫፍ ላይ ተቀመጥኩ...

አባቴ ብድግ ብሎ ወደበሩ አመራ ጥቂት በዝምታ ቆመ...

“አቢ እትዬ ማክዳ ልጆቻቸውጋ ጠቅልለው ሄደዋል...”

ማናቸው እትዬ ማክዳ ልል ነበር...

አባዬ ጥርሱን ነክሶ ጭንቅላቱን ላይና ታች በእርጋታ ነቀነቀና እጁን ጃኬቱ ኪስ ውስጥ ከተተ። መልሶ አወጣ... እግሮቹ እየመሩት ከቤት ወጣ።

የነልሳን

“የኔ ውሻ...”

ቸኮሌት ይዘዋል በእጃቸው...

“ደህና ናችሁ?... ቅዳሜ ጠዋት ና ስላሉኝ ነውኮ ይኸው መጣሁ...”

“በቃ ከእዚህ በኋላ እቤት እያስፈቀድክ ቅዳሜ ጠዋት እኔጋ ና እሺ...”

እጄን ካለበት ወደእሳቸው ወሰድ አደርገው ሶስት የተለያየ አይነት ቸኮሌት መዳፌ ላይ አስቀመጡልኝ...

ከዚህ ቀን ጀምሮ ለምላሴም ለነፍሴም የጣፈጠ ጊዜ ሆኖልኛል። ስጋዬ ልዩ ቸኮሌታቸውን ስለሚቀበል፤ ነፍሴ ልዩ ፍቅራቸውን ስለምትሸለም ልጅነቴ ታደሰ።

ምንም ያልጎደለብኝ እንደሆንኩ ይበልጥ የሚሰማኝ የሆንኩት የነልሳን እናት በጥቂት መገናኘት የሚያሳዩኝን ስስት ሳይ ነው...

...ተማሪዎች ሁሉ የሚቀኑበት የእጅ ሰአት አለኝ። ከኢቫ ቀጥሎ እኛ ክፍል አይን የሚጣልበት ነገር የእኔ የእጅ ሰአት ነው። ከየት መጣ? የነልሳን እናት አይደሉ በአንዱ ቅዳሜ እጄ ላይ ያሰሩልኝ።

“ይኸው በቃ አሁን ስትንቀሳቀስ ከበፊት ይበልጥ ጊዜህን በአግባቡ ለመጠቀም ሰአት ታያለህ...” አሉኝ “ጥናት ከስንት ሰአት እስከስንት ሰአት አጠናለሁ?፤ እስከስንት ሰአት እጫወታለሁ?፤ መንገድ ላይ ራሱ ሰው ሲጠይቅህ መልስ ይኖርሃል እሺ...”

“እሺ...”

አንዲት የሰፈራችን ሴትዮ “እትዬ ማክዳ” ብለው ተጣሩ...

ባልጠበኩት መልኩ የነልሳን እናት ናቸው ሰላምታውን የመለሱት።

አዎ! አዎ!

አሁን አባዬ ሄዱ ያለኝ፤ እትዬ ማክዳ ያለኝ፤ የነልሳንን እናት ነው።

እንዴዴዴዴዴዴዴዴ.... ወይኔኔኔኔኔኔኔኔ....

ጉድ ሆኛለሁ...

አይኔ እንባ አቀረረ...

እማዬ ትኩረቷ እኔ ላይ አይደለም። ብድግ ብላ ወደኩሽና ልትሄድ ወደበሩ አመራች። የምታስቀምጠው እቃ እንዳለ ሲገባት መለስ ብላ ወደደረቷ እጇን ከታ የተጣጠፈ ፖስታ አወጣች።

“ቅዳሜ ገበያ እንሄዳለን የምትፈልገውን ጫማ መርጠን እንገዛለን ለእኛም ለአንተም የነልሳን እናት ስጦታ ሰጥተውን ነው የሄዱት...”

እማዬ ብሩን ለማስቀመጥ ጓዳ ገባች።

ከጓዳ ሆና ድምጿ ይሰማኛል...

“እግዚአብሔር ይባርካቸው እንዴት ያሉ አሳቢ ናቸው!...”

እኔ ግን ሁሉ ጥንቅር ብሎ ቀርቶብኝ የነልሳን እናት ቢመለሱልኝ ደስታዬ ነበር... እንባዬ ወረደ።

አብዝቼ ከወደድኩት ሰው በግድ መራራቅን አንድ ብላ ሕይወት አስተማረችኝ...

አጎንብሼ እትዬ ማክዳ የገዙልኝን ሰአት ታስሮ ባለበት - እጄ ላይ አየሁት።

ጊዜ ሆይ ብትበር - ብትከንፍ ጊዜ ሆይ
ወደናፈቀኝ ሰው - ታደርሰኝ ይሆን ወይ?
(ምናለ በቀረ መሄድህ ወደፊት
ይልቅ ተመልሰህ በኖርኩ እንደበፊት...)

እንባዬ የሰአቱ መሃል መስታወት ላይ ጠብ አለ።

ይሄ ሰአት ጊዜን መቁጠሪያ ሳይሆን ማስታወሻ ነው መሆን ያለበት! ከእጄ ላይ ፈትቼ ወደጓዳ ገባሁ።

“እማዬ እስከማድግ ይሄንን ጥሩ ቦታ አስቀምጪልኝ... ሳድግ ትሰጪኛለሽ አደራ!”

~              ~            ~

ተጠናቀቀ
(መልካም ማደግ!...)

✍? በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

4 months, 1 week ago

<<የነልሳን እናት...>>
ክፍል ፱

አስቤ የማላውቀው እየሆነ ነው የማድገው...

ከጥቂት ሰላምታና ጨዋታ በቀር ከቆንጆዋ ልጅ ከኢቫጋ እንዲህ እንቀራረባለን ብዬ አስቤ አላውቅም - ተቀራረብን።

ከሳምንቱ ቀናት ቢያንስ በአንዱ ላላያት ከልሳንጋ እንዲህ እንራራቃለን ብዬ አስቤ አላውቅም - ተራራቅን።

ቅዳሜ የሳምንቱ አንዱ ቀን ሳይሆን ለእኔ ተብሎ ከእግዚአብሔር የተላከ ልዩ ቀን እስኪመስለኝ እንድደሰት የሚያደርጉኝ እናትስ?

እቤት ከትምህርት ቤት ደክሞኝ ስገባ ነው...

እናትና አባቴ ትክዝ ብለው ተቀምጠዋል ሶፋ ላይ...

ዝም ብዬ ዩኒፎርሜን ቀይሬ መክሰስ ካለ ይሰጠኝ እንደሆነ ለማየት አልጋችን ጫፍ ላይ ተቀመጥኩ።

ትካዜ ምን ማለት እንደሆነ እስከጥግ እስኪገባኝ ድረስ ቤተሰቦቼ ተክዘዋል - ቤታችን በዝምታ ተውጧል። አርፎ ቤቱ የማይቀመጠው የጎረቤታችን ድመት በለመደበት የአጥር ቀዳዳ ሾልኮ ይመስለኛል እኛ ግቢም ገብቶ እንደሌሎች ተከራይ ጎረቤቶቻችን በራችንን አነፍንፎ አለፈ።

የሆነች ዝንብ መተከዝ ከብዷት ይመስለኛል በ‛ዝንበኛ’ እየተዋከበች ነው...

“አቢዬ...”

"አቤት...”

"አንተን ፍለጋ ሰው መጥቶ ነበር...”

"ማን?”

"የነልሳን እናት...” አለች እናቴ...

“ከዛስ?”

የልጅ ልቤ በድንገት ተረበሸ... መቆሜን ያወኩት ወደበራችን ስራመድ ነው...

“ባገኘው ደስ ይለኝ ነበር አሁን ትምህርት ቤት ነው የሚሆነው በርግጥ አሉንና...”

እማዬ አውርታ ሳትጨርስ ወደእነልሳን ቤት ተፈተለኩ።

በሩጫዬ ሁሉ የነልሳን እናት ፊቴ ድንቅ እያሉ ገሰገስኩ።

በራቸው ራቀኝ...

ውሻዬ የሚል ጥሪያቸው ናፈቀኝ...

አንድ ቀን ሰፈር ውስጥ ከማልችለው ልጅጋ ተጣልቼ... ጠባችን ወደድብድብ ተቀይሮ እኔን ወደመሬት ለማፍረጥ ሰከንድ ሳይፈጅበት ዘርሮኝ ሲያበቃ ላዬ ላይ ተከምሮ በቡጢ ሊለኝ ሲል ፊቴን በሸፈንኩበት የመኪና ‛ክላክስ’ ሰማን...

ልጁም ጠቡን ረስቶ ወደእኛ የቀረበውን መኪና ሲመለከት በችኮላ ከመኪናው ወጥተው የገላገሉን ነጂ የነልሳን እናት ነበሩ። ልጃቸው ይመታ ይመስል ልጆች ሁሉ ግራ እስኪገባቸው እኔን ወደመኪናቸው ከተው ደብዳቢዬን በአጭሩ መክረው ቤታቸው በር ላይ ወስደው ዩኒፎርሜን አራገፉልኝ

“አትጣላ!”

“ራሱ ነውኮ...” እልህ ወሮኛል...

“ከማንምጋ እንዳትጣላ ከዚህ በኋላ...”

“እ እሺ...”

“ሲሰድቡህ አንተ መልሰህ አትስደባቸው ሲያድጉ ወይ አንድ ቀን ልክ እንዳልሆኑ ይገባቸዋል ቂም ሳትይዝ እለፋቸው... እሺ የእኔ ውሻ...”

ጭንቅላቴን ላይና ታች ወዘወዝኩ።

ሩጫዬን ገትቼ በራቸውጋ ስለደረስኩ ተረጋጋሁ... አተነፋፈሴ እየተዛባም ቢሆን አንኳኳሁ...

ተከፈተልኝ...

ግን ያቺው ሴት ናት ፊቴ ድቅን ያለችው።

አንድ የማታውቀው መንደር ሄዳ ከቆሻሻ ገንዳ ብቅ ብሎ ነጭ ቀሚሷ ስር እንደተገኘ ውሻ የምታየኝ ሴትዮ...

በፍፁም ይህቺማ የነልሳን እናት ዘመድ አይደለችም!

~              ~            ~

ነገ የመጨረሻው ክፍል ይለቀቃል...

✍? በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

6 months, 3 weeks ago

<<...ፀሃይ...>>

“ፀሃይ ትመስለኛለች...”

"እኔን ወንድሜ ሴቶችኮ ያቃጥላሉ ፀሃይ ባትመስልህ ነበር የሚገርመኝ...”

“ቀልድ አንተ...”

"ከልቤ ነው ባክህ ምን እልቀልዳለሁ...”

እሷን እያሰበ ፈገግ አለ...

ጣልቃ ገባበት...

“አሁን ግን የት ናት?”

"ምን አውቄ ብለህ...”

“ታድላ የት እንዳለች ሳያውቅም በፅኑ የሚወዳት ሰው አለላት”

"ተው አትቅናባት... ምናልባት አንተንም እንዲህ የት እንዳለህ ሳታውቅ የምትወድህ ትኖር ይሆናል”

“የለችም... እኔ እድሌን በደንብ አውቀዋለሁ... በዛለይ እኔ የሩቅ ፍቅር ምናምን ብዙ አይመስጠኝም...”

"ሞኝ...”

"አቤት?”

የቢሮው መስኮትጋ ወደተቀመጠው ወዳጁ ተጠጋ...

“አቤት አባባልህ ደስ ይላል... ምንም ሆነ ምን ግን ፍቅር ደስ ይላል እሺ አቤት ባዩ ወንድሜ”

ፈገግ አለ...

“አንተ”

"እ?”

“ለካ ወደህ አይደለም ቦታህን ወደዚህ ቀይረህ እዚህ'ጋ ተቀምጠህ የቀረኸው”

"ማለት”

"በዚህ መስኮት ወደውጪ ሲታይ ደስ ይላል እንደዛሬ አስተውዬው አላውቅም...”

"አዎ ኣ ደስ ይላል በጣም...”

"ኧረ ፀሃዩዋ ስታምር ወገግ ብላ ስትወጣ”

“እንዲህ ነውኮ ያልኩህ... እሷም የጠዋት የክምረት ፀሃይ ትመስላለች።”

~              ~            ~

✍? በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

6 months, 3 weeks ago

...

“ካንተጋ ነው መሄድ የምፈልገው...”

"ወዴት?”

ኩርፊያ...

ጥቂት ዝምታ...

ብድግ ያለውን እርሱን ተከትላ ብድግ አለች...

አያት ማንም ምንም ቢላት አርፋ የምትቀመጥ አትመስልም።

እንባ ባቀረሩ አይኖቿ ኮቴውን ተከተለች...

እየሄደ መሆኑ ብቻ ሳይሆን እየራቀ መሆኑ በተሰማት ቅፅበት ሮጣ በራቸው'ጋ ደረሰች...

እውነትም ገና ካሁኑ እየራቀ ነው...

መከፋት የተጫነው ድምጿን ከፍ አድርጋ እንዲህ አለች።

“ከአንተጋ ነው መሄድ የምፈልገው...”

ዞረ...

“ወዴት እንደምሄድ ታውቂያለሽ?”

"አላውቅም...”

"እና የእኔ ንፁህ ነፍስ?”

“ግን በቃ ከአንተጋ ልሂድ...”

ለማሳዘኗ ፈገግ አለላት።

በሩ ስር የተቀረቀረ ነጠላ ጫማዋን ፈልቅቃ አወጣውችና፤ በችኮላ የልጅ እግሯን አጥልቃበት ሮጣ ተከተለችው። እንባዋ ከአይኖቿ ብቻ ሳይሆን ከትንሽዬ ልቧም መድረቅ ጀመረ...

~              ~            ~

✍? በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

6 months, 3 weeks ago

<<...ሰበብ...>>

በእርምጃቸው መሃል...

እጆቿን አጎንብሶ አያቸው...

አላየችውም... አይኖቿ ጎዳናው ላይ በዝግታ መንከራተት አላቆሙም...

እሱም ቀና አለ...

መንገዳቸውን እንደቀጠሉ ነው...

የእጁን ጣቶች በአየሩ ላይ እያራመደ ወደእጇ መራቸው...

አልደከማትም... በጥቂቱ የፈካውን ሰማይ ስታይ ፈገግም አለች።

ይፈራ የለ እጁን ወደራሱ ሰበሰበ።

“ምነው ዝም አልክ?...”

“እ?... አንቺም... አንቺም ዝም ብለሻል”

ጎኗ የሚራመደውን እሱን አየችው...

መራመዱን ቀጠለ...

“ደርሰሻል...”

“እሺ በል ደህና ሁን...”

ሄደች።

በዚህች ብዙ በምታስቀይም፤ በምታስመርርና በምትጠላ አለም ውስጥ ጥቂት የሚያሳሳና ለመኖር የሚያነሳሳ ስውር ሰበብ አለ... ለእሱ ከሰበቦቹ አንዱ ይሄ ቀዝቃዛ ስንብት ነው።

~              ~            ~

✍? በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

6 months, 4 weeks ago

...

“ሊሆን ይችላል...”

“ሊሆን ይችላል አትበል ይሆናል በል...”

"እንዴ ገና ምንም የታወቀ ነገር በሌለበት...”

"እኮ የታወቀ ነገር ሳይኖር አንተ ምን አውቀህ ነው ጥርጣሬ ላይ እንዲህ ክችች ያልከው... አርፈህ ይሆናል በል...”

"እህ እኔ እንደዚህ አይነት ነገር ደስ አይለኝም...”

"አየሃ ችግርህን...”

"ምን ልትል?”

"ያንተ ችግር አንተ ራስህ ነህ...”

"እሱን መች ካድኩ የብዙዎቻችን ችግርኮ ራሳችን ነን... አንተ ግን አሁን ከራስህ አልፈህ እኔም ላይ ችግር ለመሆን እየሞከርክ ነው...”

"የራስህ ጉዳይ ለውጥ ካልፈለክ እንዲህ መቀጠል ትችላለህ...”

ዝም ተባባሉ...

እጅግ በስሱ ተኮራረፉ...

"ታያለህ ግን ያኔ ሲሳካ እኔ ብቻ ነኝ ብዬ ነበር ማለት የምችለው... አንተ ሊሆን ይችላል ብቻ ማለትህን እንዳትረሳ...”

"ኣሃ ኣሃ አንተ!... ብለን ነበር እንድንል ፈልገህ ነው እንዴ አሁን የምታደርቀኝ...”

"አፈርኩብህ ወንድሜ... ጨርሶ ብሩህ እይታ እንደሌለህ እንዴት እስካሁን አልተገለጠልኝም...”

"ምናልባትም ሰዎች ሁሌም ሁሉ ነገር ላይ ብሩህ ትንበያ ብቻ ይሰጣሉ ብለህ ስለምትተነብይ ነዋ የሚሆነው...”

“መልካም ቀን እሺ... ዞር በል በቃ ከሱቄ ላይ...”

“ሲጀመር የስራ መግቢያ ሰአቴ እየደረሰ ነው እዚህ ቆሜ ላንተ ደንበኛ ስስብ ልውል አላቀድኩም በል ደህና ዋል...”

"ካንተ'ጋ ለሚሰሩት አዘንኩላቸው ሂድ ሰላም ሁን...”

ዞር ብሎ ስቆ አይቶት መንገዱን ቀጠለ።

~              ~            ~

✍? በየአብስራ ፀጋ
YOUTUBE  TIKTOK INSTAGRAM

We recommend to visit

ይህ የቲክቫህ (ተስፋ) ኢትዮጵያ ቤተሰብ አባላት መሰባሰቢያ እንዲሁም የመረጃ እና የመልዕክት መለዋወጫ መድረክ ነው።

@tikvahuniversity
@tikvahethAfaanOromoo
@tikvahethmagazine
@tikvahethsport
@tikvahethiopiatigrigna

#ኢትዮጵያ

Last updated 2 months, 3 weeks ago

Last updated 2 months, 2 weeks ago

ይህ ስለ Manchester United መረጃዎችን የሚያገኙበት የ Telegram ቻናል ነው 🇪🇹
--------------------------------------------------------------
☞︎| ስለ ማንቸስተር ዩናይትድ ትኩስ መረጃዎች
☞| ቀጥታ ስርጭቶች ከየስታድየሞቹ
☞| የዝውውር ዜናዎች
☞| ስለ ማንችስተር ዩናይትድ ታሪኮች

📩 ለማስታወቂያ ስራ DM :- @Marcoabdu

Last updated 1 month, 2 weeks ago