Welcome To Amharic films Best Place To find Amharic Movies
አዳዲስ እና የድሮ አማርኛ ፊልሞችን እና አማርኛ ተከታታይ ድራማዎችን ለማግኝት ቻናላችንን Join ይበሉ ።
Share:- @Amharic_Films
ለማስታወቂያ - @Abusheymc & @Alpha6249
Buy ads: https://telega.io/c/Amharic_films
Last updated 1 year, 8 months ago
ስለ መድፈኞቹ የሚወጡ መረጃዎች ለማግኘት የትም መሄድ አያስፈልግም
- የዝዉዉር ዜና
- የአሰልጣኞች አስተያየት
- የተጨዋቾች የህይወት ታሪክ
- ጨዋታዎችን በቀጥታ ስርጭት
ለማስታወቂያ ስራ --> @Aymu_xo
Last updated 3 weeks, 1 day ago
╔╦╦═╦╔╦═╦═╦═╗
║ እንኳን ደህና መጡ | |
╚══╩═╩═╩╩╩╩═╝
➟ እንኳን ወደ ትልቁ የሊቨርፑል ( መርሲሳይድ) ቻናል በደህና መጡ ።
◉ ስለ ሊቨርፑል ◉
? ዝውውሮች
? ውጤቶች
? የጨዋታ ፕሮግራሞች
? እንዲሁም የተጨዋቾች ግለ ታሪክ
? ጨዋታዎችን በቀጥታ ወደናንተ የምናደርስ ይሆናል።
Owner:- @hackersolo0⭐️
Last updated 2 months, 2 weeks ago
እውነታ ሁሌ እንደምናስበው አይደለም!
(Reality is not always what we think)
(እ.ብ.ይ.)
አንዳንድ ጊዜ የምናየው የምናስበውን አይደለም፤ የምናስበውም የምናየውን አይሆንም፡፡ የምናየው ራሱን የምናየውን የሚሆንበት ጊዜ አለው፡፡ በዓይን የሚገለጥም የማይገለጥም እውነት አለ፡፡ እያየነው የማንገነዘበው ብዙ ነው፡፡ አስበነው፣ መርምረነው፣ አጥንተነውም የማንደርስበት የትየለሌ ነው፡፡ አስበን የምናገኘው አዕምሯችን ከኋላ ታሪካችን ወይም ከእውቀት ማህደራችን አገላብጦ የሚያመጣልንን መረጃ ነው፡፡ የምናየው ግን ራሱን የቻለ እውነታ ነው፡፡ እውነታውን እንደሆነው መተርጎም ወይም መረዳት መቻል ጥበብ ይጠይቃል፡፡ ጥበቡም ከአመለካከታችን አጥር ወጥተን፤ ከጠባቡ ሳጥናችን አፈንግጠን በነፃና በሰፊ አዕምሮ ማሰብን የሚጠይቅ ነው፡፡ በርግጥ አንዳንድ እውነታ በራሱ ሊነግረን የማይችለው ነገር አለው፡፡ ሔራክሊተስ እንደሚለው ‹‹የአንድ ነገር እውነተኛ ተፈጥሮ ራሱን የመደበቅ ዝንባሌ አለው (A thing’s real nature has a tendency to conceal itself)›› እንዲል አንዳንድ እውነታ የገዛ ራሱን እውነት ይደብቃል፡፡ ያን ጊዜ ከዚህ በፊት ባከማቸነው እውቀት ተመርኩዘን ካለፈው ጋር እያስተያየን እውነታውን በማጥናትና በመተንተን እውነቱን ለመረዳት እንሞክራለን፡፡ ኒኮላይ ቤርድያቭ (Nikolai Berdyaev) የተባለ ሩሲያዊ ፈላስፋና የስነመለኮት ተመራማሪ ደግሞ ‹‹እውነት ሁለት ትርጉሞች አሉት፡፡ አንደኛ እውነት በእውነታ እውቀት የሚታወቅ ሲሆን ሁለተኛ ግን ራሱ እውነታው እውነት ሆኖ ሲገኝ ነው (Truth has two meanings: there is truth as knowledge of reality, and truth as reality itself.)፡፡›› ይላል፡፡ አዎ የሚታየውን አይቶ፣ የሚሰማውን ሰምቶ መረዳት መቻል ትልቅ ችሎታ ነው፡፡ ብዙዎቻችን የምናየውን የምንረዳው ነገርየው እንደሆነው ሳይሆን ከዚህ ቀደም ከነበረን ብጫቂ መረጃ በመነሳት ነው፡፡ በብጫቂ መረጃ ነገሮችን መደምደም ደሞ ስህተት ላይ ይጥላል፡፡ እውነታን እንደምናየው መበየን ካልቻልን ከዚህ ቀደም በተጫነብን መረጃ እንፈርጀዋለን፡፡
Psychology Today የተባለ ድረ-ገፅ ከትናንት በስቲያ በፈረንጆቹ የካቲት 8 ቀን 2025 ዓ.ም. ባወጣው ፅሁፉ ‹‹ለምንድነው የሰው አንጎልና ሰው ሰራሽ ክህሎት (AI) እውነታን የሚገነዘቡት እወነታው እንደሆነው ሳይሆን በግምት ዕውቀት የሆነው? (Why AI and the brain perceive only what they predict, not what's actually there)›› ብሎ በመጠየቅ እውነታውን የምንረዳበት መንገድ የተሳሳተ ስለመሆኑ ብዙ ትንታኔዎችን ያስቀምጣል፡፡ ልክ ነው የዘመናችን የAI ቴክኖሎጂ ተመሳስሎ የተሰራ የሰው አዕምሮ ቅጂ ነው፡፡ አዕምሯችን መረጃዎችን እንዴት እንደሚያደራጅና እንደሚያስተሳስር ለማወቅ ለፈለገ ሰው የAI ቴክኖሎጂዎችን ማየት በቂው ነው፡፡ ሰውና ሮቦት ሁለቱም እውነታን የሚገነዘቡት በግምት ዕውቀት ነው፡፡ የግምት ዕውቀት ማለት ከዚህ ቀደም በአዕምሯችን ውስጥ በተከማቸው መረጃ ተመርቶ እውነታውን መበየን መቻል ማለት ነው፡፡ ይሄ ሂደት በAI የተለመደ ነው፡፡
በዘመናዊው የዳታ ሳይንስ Data Mining የሚባል የትምህርት መስክ አለ፡፡ Data Mining ማለት በአጭሩ የተከማቸን መረጃ በትንበያና እርስበርስ በማስተሳሰሪያ (Predictive and/or associative model) ዘዴ በመጠቀም፣ በቅደም ተከተል በመደርደር (sorting) እና የመረጃዎቹን አንድዓይነትነትና የእርስበርስ ትስስር (identify patterns and relationships) በማጥናት አዲስ እውቀት ወይም እይታ (Insights) የመፍጠሪያ ሂደት ነው፡፡ በርግጥ AI የሰውን አዕምሮ ያህል ችሎታ የለውም፡፡ AI ባለው መረጃ ውስን ነው፡፡ ከዛች መረጃ ተነስቶ ነው እውነታን በትንበያ ዕውቀቱ የሚገነዘበው፡፡ ትንበያው ልክ ሊሆንም ላይሆንም ይችላል፡፡ አዕምሯችን ግን ካለው መረጃ ባሻገር ከዕውቀት መዝገቡ ያልተቀመጠ በስሜት ሕዋሱ አማካኝነት አዲስ መረጃም ሲያገኝ የማሰላሰልና የማገናዘብ አቅም አለው፡፡
አዎ ዓይን የሚያየውን ሁሉ ማመን አደገኛ ነው፤ በአንፃሩም አዕምሮ ያሰበውን ሁሉ ማመንም የበለጠ አደገኛ ነው፡፡ አይን የማያየው ልብ ብቻ የሚመለከተው ብዙ ነገር አለ፡፡ አዕምሮም የማይደርስበት የስሜት ሕዋሳችን ብቻ የሚነግረን መረጃም የትየለሌ ነው፡፡ ግምታችንን የሚያሳስቱ ብዙ ሃሳቦች አሉ፤ እንደዚሁም የስሜት ሕዋሳታችን የሚሰጠን መረጃም የመጨረሻው እውነት አይደለም፡፡ ትክክሉ ያለው መሐሉ ላይ ነው፡፡ ብልህ ሰው ከስሜቱም ከአዕምሮውም ወጣ ብሎ ማሰብ ሲችል ነው ከሁለቱም ፅንፎች ሊፈጠሩ የሚችሉ የተሳሰቱ ግንዛቤዎችን ማስወገድ የሚችለው፡፡ ወጣ ብሎ ማሰብ የሚቻለው ከሳጥን ውጭ ማየት ሲጀመር ነው፡፡ ለዚህም ሰፊ አዕምሮ (Extended mind) ያስፈልጋል፡፡ በራስ ትንሽዬ መስኮት አጮልቆ ማየት ብቻ ሳይሆን የሕሊናን በር በርግዶ በመክፈት ሰፊውን ዓለም በሙላት ማየት ሲቻል ነው እውነታውን በትክክል መገንዘብ የሚቻለው፡፡ በሙላት ማየት ማለት ያለምንም ቅድመ ደጋፊ ዕውቀት ወይም ጥገኛ ሃሳብ የምናየውን በነፃነት ማየት መቻል ማለት ነው፡፡ ወይም አሁን የምናየውን ከዚህ ቀደም ከምናውቀው ዕውቀት ጋር ሳናገናኝና ሳናዋህድ ነገርየው በራሱና በራሱ ብቻ በቀጥታ መገንዘብ መቻል ነው፡፡ ይሄም ያለፈው ልምዳችን እውነታውን እንዳያዛባብን ያደርጋል፡፡ እውነታውን የምናዛምደው እውነታውን በነፃ ምልከታ ከተረዳነው በኋላ ሲሆን አመለካከታችንንና ግንዛአቤያችንን የተሻለ ያደርጋል፡፡ አለበለዚያ ትናንት ከምናውቀው ተነስተን አዲሱን እውነታ ለማወቅ ከሞከርን የምናገኘው መረጃ ፍፁም እውነት አይሆንም፡፡
ወዳጄ ሆይ… ኒቼ (Neitzche) ‹‹ንጹህ አየር በሌለበት ሁኔታና ከእንቅስቃሴ ነፃ ባልሆነ ስፍራ ያዋለድከውን ሃሳብ አትመነው (do not believe any idea that was not born in the open air and of free movement)›› የሚለው ወድዶ አይምሰልህ፤ ነፃ ሃሳብ ነፃነትን ስለሚፈልግ ነው፡፡ የሆነ የአስተሳሰብ ጥግ ላይ ተቸክለህ የምታስበውም ሃሳብ ዓየሩ የተበከለ ስለሆነና የሆነ አስተሳሰብ ጥገኛ ስለሚሆን የምትተማመንበት ትክክለኛ ሃሳብ ማፍለቅ አትችልም፡፡ ትክክለኛ ሃሳብ ማሰብ ከፈለግክ ከምትደግፈው፣ ከምትወደው፣ ከፖለቲካ ርዕዮትህ፣ ከሃይማኖት ቀኖናህ፣ ከጎጥህ፣ ከፍልስፍናህ፤ ከልማድህ፣ ከባህልህ፣ አዕምሮህ አግበስብሶ ካከማቸው መረጃህ ራቅና ገለል ብለህ በነፃነት ማሰብን ተለማመድ፡፡ ያን ጊዜ እውነታውን በሙሉ ዓይንህ ታየዋለህ፣ በሙሉ ሃሳብህ ትረዳዋለህ፣ በንፁህ ልቦናህ ትገነዝበዋለህ፣ በነፃ ሕሊናህ ትተነትነዋለህ፡፡ ከዛም ከእምነትህ፣ ከፍልስፍናህ፣ ከባህልህ፣ ከሌላም ከሌላም ነገርህ ጋር ታወዳጀዋለህ፣ ትዋጀዋለህ፡፡
ቸር ዕይታ! ልክ እውነታ!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
________________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ የካቲት ፫ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
ሳይታሰቡ የሚታመኑ ነገሮች እምነታችንን አያጠነክሩትም፡፡
(The art of remaining uncertainity)
(እ.ብ.ይ.)
አንዳንድ ሰዎች በደንብ ባላወቁት፣ ባላጠኑትና ባልመረመሩት ነገር እርግጠኞች ናቸው፡፡ ጫፍ ጫፍ የሚያውቁትን ነገር ሁሉ ብቸኛው እውነት እሱ ነው ብለው ይደመድማሉ፡፡ የማያውቁትንና ያልመረመሩትን ደግሞ ስህተት ነው ብለው በጭፍን ይፈርጃሉ፡፡ የምታውቀውን ብቻ እውነት፣ የማታውቀውን ውሸት የምትል ከሆነ ውሸቱም ሆነ እውነቱ አንተ በአስተሳሰብህ የፈጠርከው ነው፡፡ መርማሪ አዕምሮ ከሌለህ ላንተ የሚስማማህን ሃሳብ ሁሉ እውነት፤ የማታውቀውን ደግሞ ስህተት ትላለህ፡፡ በዘመናችን የምናየው የኢአማኞችና የሃይማኖተኞች እንዲሁም የፖለቲከኞቻችን ንትርክ የዚህ አካል ምሳሌ ነው፡፡ የእኔ ብቻ ነው ልክ የሚል አባዜ፡፡ የሌላውን ለመረዳት አንዲት እርምጃ የማይራመድ ሰው ነው በርግጠኝነት የሚናገረው፡፡ አሜሪካዊው ፀሐፊ ሮበርት ግሪን አነጋጋሪና አወዛጋቢ በሆነው “The 48 Laws of Power” በተባለ መፅሐፉ ‹‹ሰዎችን አላዋቂ የሚያደርጋቸው ለሁሉም ነገር መልስ አለኝ የሚል እርግጠኝነታቸው ነው (What makes peoples stupid is their certainity that they have all the answers)›› ይላል፡፡ ሮበርት ግሪን ለዚህ ንግግሩ ምሳሌ የሚያቀርበው አቴናውያን በፔሎፖነስያን (Peloponnesian War) ያደረጉትን ጦርነት በመጥቀስ ነው፡፡ የአቴናውያን መሪዎች ጦርነቱን በሙሉ ርግጠኝነት እናሸንፋለን ብለው ነው ወደጦርነት ሜዳው የገቡት፡፡ የበዛ እርግጠኛነታቸው ግን ጉድ ሰርቷቸዋል፡፡ ተሸንፈው ወርቃማውን የአቴናውያንን ዘመን ቋጭተዋል፡፡ ለዚህ ነው ግሪን ‹‹በነገሮች ፍፁም እርግጠኛ የሚሆኑ ሰዎች አላዋቂዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች ስልጣን ከያዙ እጅግ በጣም አደገኛ ነው የሚሆኑት (“People who are certain of things are very stupid, and when they have power, they’re very, very dangerous)›› የሚለን፡፡
ብዙ ሰዎች ባመኑት ሰው ተከድተዋል፡፡ ርግጠኛ በሆኑት ነገር ተሸንፈዋል፡፡ ይሆንልናል ብለው መቶ በመቶ በተቀበሉት ነገር አንገት ደፍተዋል፡፡ እናውቃለን፣ ልክ ነን ብለው ሙሉ ልባቸውን ሰጥተው ልባቸው የተሰበረ ጥቂት አይደሉም፡፡ እንግሊዛዊ ገጣሚ የነበረው ጆን ኬትስ (John Keats’) ለዚህ መድሐኒት አለኝ ይላል፡፡ መድሐኒቱም በእሱ አገላለፅ “Negative capability” ይለዋል፡፡ Negative capability ማለት ለነገሮች ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ አለመሆን ነው፡፡ ወይም ደግሞ በአንድ ጉዳይ ላይ በተመሣሣይ ጊዜ ሁለት ተቃራኒ ሃሳቦችን ጭንቅላታችን ላይ የማስቀመጥ ችሎታ ማለት ነው (“hold two thoughts in your head at the same time, two thoughts that apparently contradict each other.”)፡፡ በሌላ አገላለፅ በአንድ ጊዜ ይሆናልንም አይሆንምንም ማሰብ እንደማለት ነው፡፡
በአሜሪካ ምዕራብ ፔንስላቫንያ ግዛት ውስጥ የሚገኝ ፒተስበርግ በተባለ ከተማ ውስጥ ጥር 6 ቀን 1995 ዓ.ም. የተፈፀመ አንድ ወንጀል ለዚህ ሃሳብ ጥሩ ምሳሌ ሊሆነን ይችላል፡፡ ወንጀሉ ማካርቲ ዊለርና ከሊፍተን ኸርል ጆንሰን የተባሉ ሁለት ግለሰቦች የባንክ ዝርፍያ የፈፀሙበት ታሪክ ነው፡፡ ሁለቱም ሰዎች የሎሚ ጭማቂ ፊታቸውን በመቀባት የደህንነት ካሜራዎችን ማለፍ እንደሚችሉ እርግጠኛ ሆነው ነበር ወደዝርፊያው ያመሩት፡፡ ጆንሰንና ዊለር የደህንነት ካሜራው ላይ እያሾፉና እየቀለዱ ወደባንኩ በመግባትና በጦር መሣሪያ በማስፈራራት በጊዜው 5200 ዶላር ዘርፈው ተሰውረዋል፡፡ የሆነው ሆኖ ግን የሎሚ ጭማቂው ማንነታችንን አያሳይም ብለው መቶ በመቶ አምነው የነበረ ቢሆንም ከፖሊስ አደና ግን ራሳቸውን ማትረፍ አልቻሉም፡፡ ጆንሰን ወዲያው ከ6 ቀናት በኋላ ሲያዝ ዊለር ግን በደህንነት ካሜራው የቪዲዬ ጥራት ቴክኒካል ችግር ምክንያት ማንነቱን ለመለየት ትንሽ አስቸግሮ የነበረ ቢሆንም ከሶስት ወር በኋላ ግን ሊያዝ ችሏል፡፡ በነሱ ቤት ስማርት መሆናቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ማንም አያውቅብንም ብለው ርግጠኛ ሆነው የተጠቀሙት ዘዴ ፍርደኛ ከመሆን አላዳናቸውም፡፡ የስነልቦና ባለሞያዎች ይሄንን ጉዳይ Dunning-Kruger effect ይሉታል፡፡ Dunning-Kruger effect ማለት በፈረንጆቹ 1999 ዓ.ም በሳይኮሎጂስቶቹ ዴቪድ ዱኒንግና ጀስቲን ክሩገር አማካኝነት የተቀነቀነ አስተሳሰብ ሲሆን ትርጉሙም ሰዎች በተሳሳተ ግንዛቤ ራሳቸውን ፍፁም እርግጠኛ አዋቂ አድርገው ሲቆጥሩ የሚፈጠር ነው፡፡ ወይም በሌላ አገላለፅ የተዛባ ግንዛቤ (Cognitive bias) ሲፈጠር የሚከሰት ነው እንደማለት ነው፡፡
ወዳጄ ሆይ… በመጠራጠር ብዙ ታተርፋለህ፤ በባዶ እርግጠኛ መሆንህ ግን የኋላ ኋላ ይጎዳሃል፡፡ መጠራጠር ለማሰብና ለመመርመር በር ይከፍታል፡፡ ከተጠራጠርክ አዕምሮህ ላይ አትቆልፍበትም፡፡ የበለጠ እንድትፈትሽ፣ እንድትመዝን፣ በአራቱም አቅጣጫ እንድታይ ያደርግሃል፡፡ አንዳንዶች መጠራጠርን እንደመጥፎ ባህርይ ይቆጥሩታል፡፡ ጥርጣሬህን በአግባቡ እስካደረግከው ድረስ ይጠቅምሃል እንጂ አይጎዳህም፡፡ ልብህን ከመሰበር፤ ውስጥህን ከመቃጠል፣ አዕምሮህን ሰላም ከማጣት የምትታርፈው የልብህን በር ገርበብ አድርገህ ስትከፍት ነው፡፡ ልብህን ከፈት፣ አዕምሮህን ገርበብ የምታደርገው ለተቃራኑ ሁነቶች ነው፡፡ ባይሆንስ፣ ባይሳካስ ብሎ ማሰብ ይሆናሉ ብለህ ያሰብካቸው ነገሮች ባይሳኩና ባይሆኑ አትደነግጥም፡፡ ምክንያቱም ቀድመህ ተዘጋጅተህበታልና፡፡ እንደውም ሌላ መውጫ መንገድ እንድታስብ ያደርግሃል፡፡ በሁሉም ነገር እርግጠኛ የሆኑ ሰዎች በመጨረሻ ሲጎዱና አንገት ሲደፉ ነው የምናያቸው፡፡ እርግጠኛ ከሆንክም በራስህ የጠራ አስተሳሰብ እርግጠኛ ሁን፡፡ በሌሎች ሰዎች ወይም በውጫዊ ነገሮች፤ አልያም በምትሰማውና በሚነገረው ሁሉ እርግጠኛ አትሁን ማለት ሰዎችን አትመን ማለት አይደለም፡፡ የምታምነውን ነገር መዝነህ፣ ፈትሸህና መርምረህ እመን ማለት ነው፡፡ ሳይታሰቡ የሚታመኑ ነገሮች እምነታችንን አያጠነክሩትም፡፡ እምነት የሚጠነክረው በእውቀት ሲሆን ነው፡፡ የምታምነውን እወቀው፤ እርግጠኛ የምትሆንበትን ነገር በደንብ አድርገህ መርምረው፡፡
ቸር ጊዜ!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
________________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጥር ፳፮ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
ቸር ድል!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
________________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጥር ፲፱ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
ችግርህን ወይ ተቋቋመው፤ ወይ ተሰቃይበት!
(Mope or Cope)
(እ.ብ.ይ.)
የብዙዎቻችን ቸግር የደረሰብንን ችግር የምናይበት መንገድ ነው፡፡ ችግሩን የምናይበት መንገድ ራሱ ችግር ነው! (The way we see the problem is the problem)፡፡ አንደኛ ከችግሩ ልንወጣበት ያሰብነው መንገድ ራሱ ሌላ ችግር ውስጥ የሚከትት ነው፡፡ መንገዱ ወደገደል ይዞን የሚገባው መውጫ መንገዱን ያየንበት መንገድ የተሳሳተ በመሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛ ችግሩን ልንፈታበት ያሰብነው መላ ትናንት በወደቅንበት መላ ነው፡፡ በወደቅንበት በኩል መነሳት ከባድ ነው፡፡ ጊዜ ባለፈበት ዘዴ አዲስ በር መክፈት አይቻልም (Old ways do not open new doors)፡፡ አዲስ እይታ፣ አዲስ መንገድ ወሳኝ ነው፡፡
ሰውየው ዛፍ እየቆረጠ ነው፡፡ አንድ መንገደኛ ‹‹ምን እየሠራህ ነው?›› ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ዛፍ ቆራጩም ‹‹የምሠራው አይታይህም? ዛፍ እየቆረጥኩ ነው እኮ!›› አለው፡፡ መንገደኛውም ‹‹በጣም የደከመህ ትመስላለህ፡፡ ምን ያህል ጊዜ ሆነህ ዛፍ መቁረጡን ከጀመርክ?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ዛፍ ቆራጩም ‹‹ከአምስት ሠዓታት በላይ ይሆናል፡፡ ከአቅሜ በላይ ሆኗል፡፡ ከባድ ስራ ነው›› በማለት ስልችት ባለ ድምፀት መለሰለት፡፡ መንገደኛውም ‹‹ታዲያ ለምን ትንሽ ደቂቃ አታርፍምና መጋዙን ሞርደህ አትቀርጥም? ቶሎ የምትጨርስ ይመስለኛል›› አለው፡፡ ዛፍ ቆራጩም ‹‹ለመሞረድ ጊዜ የለኝም›› በማለት መለሰለት ይባላል፡፡
ዛፍ ቆራጩ ጊዜ የሌለው ለሚያደክም ስራ ነው፡፡ ጊዜውን ባግባቡ ለመጠቀም አልሞከረም፡፡ ፈረንጆቹ Busy for nothing እንደሚሉት ዓይነት ነው፡፡ ድካማችንን የሚያረዝመው ለችግሩ ያለን አስተሳሰብ ነው፡፡ ጊዜን ባግባቡ መጠቀም ማለት እንደዚህ አይደለም፡፡ አምስት ደቂቃ አርፈህና መጋዝህን ሞርደህ ድካምህንና ጊዜህን መቀነስ በማሰብ የሚገኝ መላ ነው፡፡ አምስት ደቂቃ አስቦ አምስት ሰዓታትን ማትረፍ ጊዜን በአግባቡ ከመጠቀም አልፎ ከጊዜ ከራሱ ማትረፍ ነው፡፡
በዋናነት እኛን የሚጎዳን ወይም የሚሰብረን የደረሰብን ወይም እየሆነብን ያለው ነገር ሳይሆን እየሆነ ላለውና ለደረሰብን ነገር የምንሰጠው መፍትሄ ወይም ምላሽ ነው፡፡ (It is not what happens to us but our response to what happen to us that hurts us):: እንቅፋቶቻችንን ሙሉ በሙሉ ቀድመን አውቀናቸው ልናስወግዳቸው አንችልም፡፡ የምንችለው ከእንቅፋቱ በኋላ ያለውን ሁኔታ ነው፡፡ ሳንካ፣ ፈተና፣ ጋሬጣ በህይወት መንገድ ላይ ያጋጥማል፡፡ በሳንካው ወይም በጋሬጣው መሰቃየት ግን ምርጫ ነው፡፡ ከሁኔታው በኋላ ያለው ነው በእኛ አዕምሮ ፈቃድ የሚወሰነው፡፡ በደረሰብን የምንተክዝና የምንሰቃይ ከሆነ የሚተርፈን ወዮታ ብቻ ነው፡፡ የደረሰብንን ነገር ገልብጠን ወደመልካም የምንለውጥ ከሆነ ግን የምናገኘው ከችግር ነጻ መውጣትን፣ አዲስ ልምድና ደስታ ነው፡፡
የጋራ ችግሮቸቻችንም የማይፈቱት ስለማንደማመጥ ነው፡፡ ብንሰማማም አንደማመጥም፤ ብንደማመጥም አንግባባም፡፡ በቃላት የማንግባባው፣ በሃሳብ የምንለያየው፣ በጉንጭ አልፋ ክርክር ጊዜ የምናጠፋው እርስበርስ ለመግባባትና አንዱ አንዱን ለመረዳት ስለማንፈቅድ ነው፡፡ ብዙ ክርክሮቻችን ያን ያህል የሃሳብ ልዩነት የሉባቸውም፡፡ ስቴቨን ኮቪይ “Most arguments are not disagreements but are rather little ego battles and misunderstandings” እንዲል እርስበርስ አለመግባባትና ‹‹እኔ እበልጥ- እኔ እበልጥ›› የሚል በልጦ የመገኘት የግል ጦርነት ነው ልዩነታችንን እያሰፋ ያለው፡፡
ወዳጄ ሆይ..... ከችግርህ ጋር ስትሰቃይ ትኖራለህ? ወይስ ችግርህን ገንድሰህ ትጥለዋለህ? (Are you going to cope or mope?) ምርጫው ያንተ ነው፡፡ ከራስ ጋር የሚደረገው ጦርነት ቀላል አይምሰልህ፡፡ አጉል ልማድህን ድል ማድረግ፣ ለከት ከሌለው ፍላጎትህ ነጻ መውጣት፣ ስሜትህን መግራት ከቻልክ የትኛውም ችግር አያስደነግጥህም፡፡ ችግርህን ተራራ የሚያሳክለው የተሳሳተው አስተሳሰብህና ስሱ ስሜትህ ብቻ ነው፡፡ ስሜትህ ስስ ከሆነ በደረሰብህ ሁሉ ታላዝናለህ፡፡ አስተሳሰብህን ካዘመንክ፣ ስሜትህን ካጠነከርክ ግን ከችግር መውጫ መንገዱን ማግኘት አይከብድህም፡፡ መላው በእጅህ ይሆናል፡፡
በችግርህ ላይ በማላገጥ ከችግርህ መላቀቅ አትችልም፡፡ ችግርህን የሚፈታ አዲስ ሃሳብና ተግባር ግድ ይልሃል፡፡
ቸር ብልሃት!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
_______________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጥቅምት ፲፰ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
‹‹እጅና እግርን ከማጣት የአካልጉዳት በላይ ፍርሃት ትልቁ ጉዳት ነው፡፡››
(Fear is the bigger disability than having no arms and legs)››
(እ.ብ.ይ.)
ፍርሃት ተፈጥሯዊ ነው፡፡ የማይፈራ ማንም የለም፡፡ ሃብታም በለው ንጉስ፤ ደሃ ይሁን ተራ ፍርሃት ሁሉንም ያንቀጠቅጣል፡፡ ከሞት ጋር አብሮ የሚውለው፤ ነፍሱን ለሐገሩ አሲይዞ የሚዋጋው ወታደር እንኳን በፍርሃት ይናጣል፡፡ ፍርሃት ከእኛ ጋር ተፈጥሯል፡፡ ፍርሃት የወደፊቱን ያለማወቃችን ምልክት ነው፡፡ ሁሉን አለማወቅ ደግሞ ሃብት ንብረታችን ነው፡፡ ሁሉን አውቀን መጨረስ አንችልም፡፡ ከምናውቀው በላይ የማናውቀው እልፍ ነው፡፡ በርግጥ ብናውቅም ባናውቅም፤ ሊቅም ሆንን ደቂቅ፤ መረጃ ኖረን አልኖረ የሚያስፈራን ብዙ ነገር አለ፡፡ ነገር ግን ከሚያስፈራን አስፈሪው ነገር የበለጠ ራሳችን በአስተሳሰባችን የፈጠርነው ምክንያታዊ ያልሆነ ፍርሃት (Irrational In-house fear) ነው ከዓላማችን የሚያደናቅፈን፡፡ ብዙዎች በሰው ሰራሽ ፍርሃት ምክንያት ፀጋቸውን አልተጠቀሙበትም፤ ህልማቸውን እውን ሳያደርጉ ያለፉና የጋን ውስጥ መብራት የሆኑ ቤት ይቁጠራቸው፡፡ በአካል ጉዳታቸው ምክንያት በጓዳ የቀሩ ብዙ መክሊቶች አሉ፡፡
ፍርሃታቸው ቤት ካላስቀራቸው ለዓለም ሕዝብ ምሳሌ ከሆኑ ሰዎች መካከል የአንዱ ሰው ታሪክ ግን ለየት ያለ ነው፡፡ ወደዚች ዓለም ሲመጣ Tetra-ameliua syndrome ተጠቂ ሆኖ ነው የተወለደው፡፡ ይሄ በሽታ በዩኤስኤ እንኳን ከአንድ ሚሊየን ሰዎች መካከል ባንድ ሰው ብቻ የሚከሰት በተፈጥሮ የሚመጣ የእጅና እግር የማጣት የአካል ጉዳት ነው፡፡ ሰውየው የሚበላበት እጅና የሚንቀሳቀስበት እግር የለውም፤ ነገር ግን ተረከዝና ጣቱን በመጠቀም በደቂቃ እስከ 45 የሚደርሱ ቃላትን ኮምፕዩተር ላይ መተየብ ይችላል፡፡ ዋና መዋኘት፣ መኪና መንዳት፣ ከበሮ መምታት፣ ቴኒስ መጫወት፣ ሀይለኛ የባህር ሞገድ ላይ መንሳፈፍ (Surfing) አልተሳነውም፡፡ ተሰድቧል፣ ተንቋል፣ ብዙ መከራ አይቷል፤ ነገር ግን መከራውን ሁሉ ተሻግሮ ትልቅ ስኬት ላይ ደርሷል፡፡ ተስፋ ቆርጦ ራሱን እስከማጥፋት ቢደርስም ያንን ጨለማ አስተሳሰቡን አሸንፎና ራሱን ቀና አድርጎ እንደእሱ በእሱ መከራ መንገድ የሚመላለሱትን ሚሊዮኖች ምሳሌ በመሆን መንገድ አሳይቷል፤ የዓለምን ሕዝብ አነቃቅቷል፡፡ አካል ጉዳተኛ ነው፤ ነገር ግን አፍቅሮና ተፈቅሮ፣ አግብቶና ወልዶ ለመሳም አካል ጉዳቱ ምንም አላገደውም፡፡ የሁለት ወንድ እና የመንታ ሴቶች ልጆች አባት ሆኗል፡፡ እጅና እግር አልባ ሆኖ መወለዱ በቤት አስተኝቶ አላስቀረውም፤ እንደውም ዓለምን በአነቃቂ ንግግሩ አጥለቅልቋል፡፡ ራሱን አልደበቀም፤ ይልቁንስ እስከነጉዳቱ በአደባባይ ራሱን ገልጧል፡፡ ተሞክሮውን፣ ያሳለፈውን ውጣውረድ፣ በራሱና በአምላኩ ላይ ያለውን መተማመን፣ እምነትን በተግባር የመግለጥ አስፈላጊነትን፣ የፍቅር ግንኙነቱን፣ ራሱን በራሱ የጎዳበትን (Self destructive thoughts) ሃሳቡን፣ መቆጣጠር የማይችላቸው ከአቅሙ በላይ የሆኑ ክስተቶችን እንዴት ለአምላኩ አደራ እንደሰጠ፣ በአካሉ፣ በአዕምሮው፣ በልቡና በመንፈሱ መካከል ያለውን ሚዛን አጠባበቁንና ወዘተ ወደር የሌላቸው ሃሳቦቹን በተከታታይ ባሳተማቸው ሰባት መፅሐፎቹ ተሞክሮዎቹን በሙሉ ለአንባቢዎቹ አጋርቷል፡፡ መፅሐፎቹም ‹‹Life without limitation (2007)››፣ ‹‹Unstoppable: The Incredible Power of Faith in Action (2013)››፣ ‹‹Limitless: Devotions for a ridiculously good life (2013)›› ‹‹The power of Unstoppable faith (2014)››፣ ‹‹Stand strong (2015)››፣ ‹‹Love without Limits (2016)›› እና ‹‹Be the hands and feet (2018)›› ይባላሉ፡፡
ይሄ ሰው አውስትራሊያዊው አነቃቂና ወንጌላዊ የሆነው ኒክ ቩጂሊክ (Nick Vujicic) ነው፡፡ ‹‹ሰው እግዚአብሔር ካለው እጅና እግርን ማን ይፈልጋል (“Who needs limbs when you have God?”)›› ይላል፡፡ በእግዚአብሔር ላይ ያለው እምነቱ ጠንካራ ነው፡፡ በራሱ ይተማመናል፣ በአምላኩ ያምናል፡፡ እምነቱን በአፉ ብቻ ሳይሆን በተግባርም (Faith in action) ይኖርበታል፡፡ ልጆቹን አቅፎ የሚያጫውትበት፣ ባለቤቱን ዳስሶ የሚያሞቅበት እጅ የለውም፡፡ ነገር ግን ልቦቻቸውን በፍቅር የሚያቀልጥበት የሞቀ ልብ አለው፡፡
ኒክ ‹‹Unstoppable›› በተባለው ሁለተኛው መፅሐፉ በመጀመሪያው ምዕራፍ ‹‹Faith in Action›› ላይ በብዙ ምሳሌዎች እንደሚያብራራው እምነት ያለተግባር ከንቱ መሆኑን ነው፡፡ እምነትህን የሚያረጋግጠው መልካም ስራህ ነው፡፡ ሃይማኖተኝነት ወይም እምነት ትልቅ ነገር ነው፤ ነገር ግን ያንተን ሕይወት የሚለካው ሃይማኖትህ ብቻ ሳይሆን መልካም ስራህም ጭምር ነው ይላል፡፡ እግዚአብሔር እጅና እግር የሌለው አድርጎ የፈጠረኝ ሊቀጣኝ ሳይሆን ሌሎችን ማስተማሪያ እሆን ዘንድ ሊጠቀምብኝ ነው ብሎ ያስባል፡፡ ጉዳቱን ለበረከት ተጠቅሞበታል፡፡ ለዚህም ነው ‹‹በሕይወት ውስጥ አማራጮች አሉህ፡፡ መራራውን ወይስ ጣፋጩን ነው የምትመርጠው?›› ብሎ ይጠይቅና ‹‹መራራውን ትተህ ጣፋጩን ምረጥ›› በማለት ይመክራል፡፡ አዎ በሌለህ ነገር እያማረርክ ከኖርክ ሕይወትህን መራራ ይሆናል፡፡ ባለህ ፀጋ ተጠቅመህ ግን ራስህን ለመለወጥ ቆርጠህ ከተነሳህ ሕይወትህን ጣፋጭ ታደርጋለህ፡፡ ጨዋታው ያለው ጠቃሚውን መምረጥ ላይ ነው፡፡
ወዳጄ ሆይ..... ኒክ ‹‹እጅና እግርን ከማጣት የአካልጉዳት በላይ ፍርሃት ትልቁ ጉዳት ነው፡፡ (Fear is the bigger disability than having no arms and legs)›› የሚለው ራስህን ከሚጎዳህ ከአጉል ፍርሃት ራስህን ጠብቅ ለማለት ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ተሸናፊ የሆኑት ባላስፈላጊ ፍርሃት ነው፡፡ መፈራት የሚገባውን መፍራት ተገቢ ነው፡፡ የማያስፈራውን መፍራት ግን ስነልቦናዊ ህመም ነው፡፡ ፍርሃትህ ከአስተሳሰብህ፣ ከህልምህ፣ ከግብህ እንዳያቆምህ ተጠንቀቅ፡፡ ፍርሃትህን መዝነው፤ ሃሳብህን ፈትሸው፤ የምትችለውን ከማትችለው ለይ፡፡ እምነት የሚረጋገጠው በተግባር ነው፡፡ ሃይማኖት ኖሮህ መልካም ስራ ከሌለህ የምታምነውን የእውነት አታምነውም ማለት ነው፡፡ እምነትህን በተግባር ግለጥ፤ ሃይማኖትህን በመልካም ስራ አሳይ!
ቸር እምነት! ደግ ፍርሃት!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
_________________________
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ጥቅምት ፲፩ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም.
ምህዋረ ሃሳብ፦
“አውቆ አለመተግበር አለማወቅ ነው”
ጸሐፊ፦እሸቱ ብሩ ይትባረክ
አቅራቢ፦ተስፋዬ ማሞ
ሰዎች የሚናገሩትን ብቻ ሳይሆን የማይናገሩትንም አስተውል!
(Understand to what people don’t say)
(እ.ብ.ይ.)
ብዙ ጊዜ ሰው በንግግሩ ብቻ አይታወቅም፡፡ የሚናገረው ሌላ ማንነቱ ሌላ የሆነ ሰው እልፍ ነው፡፡ ሰው ከሚናገራቸው ይልቅ ድርጊቶቹ ናቸው የሰውየውን ማንነቱን የሚናገሩት፡፡ ቃል አሳሳች ነው፡፡ አፍ ወላዋይ ነው፡፡ ስሜታዊ ንግግር አይጨበጥም፡፡ ስብከት ብቻ ሰውን አይለውጥም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹አትስረቅ እያልክ የምትሰብክ ትሰርቃለህን?›› የሚለው ለዚህ ነው፡፡ ተራ ዲስኩር የሰዉን ልኩን አያሳውቅም፡፡ የሰው ልኩ ያለው ድርጊቱ ላይ ነው፡፡ ድርጊቱ ከሃሳቡ የተወለደ ነው፡፡ የሰውን ሃሳብ ማወቅ አዳጋች ቢሆንም አስተዋይ ከሆንክ ግን ከንግግሮቹ መሃል ያልተናገራቸውንና ያልገለጣቸውን ስሜቶቹን በማንበብ ልትረዳው ትችላለህ፡፡
ብዙ ሰው የእሱን እውነት አምነህ እንድትቀበለውና እንድትረዳው የማያደርገው ጥረት የለም፡፡ እሱ ግን አንተን አንድ ሰከንድ አድምጦህ ሊገነዘብህ አይፈቅድም፡፡ የማያዳምጥ ሰው ማሳመንም ማመንም አይችልም፡፡ ፕሌቶ “ሪፐብሊክ” በተባለ ስራው ‹‹የማያዳምጡ ሰዎችን ማሳመን አትችልም (You can not persuade people who won’t listen)›› የሚለው ለዚህ ነው፡፡ የማያዳምጥ ሰው ቢናገርም ንግግሩ ውሃ አይቋጥርም፤ ቢሰማምም ከልቡ አያዳምጥም፡፡ ዲስኩሩ ከማሳመን ይልቅ ደካማ አስተሳሰቡን ያሳብቃል፡፡
ሰዎች ብዙ ጊዜ ከሚናገሩት ይልቅ የማይናገሩትን ናቸው፡፡ ከተነፈሱት ይልቅ ያልተነፈሱት ነው የነሱን ትክክለኛ ማንነት የሚገልፀው፡፡ ከሚናገሩት መሀል ያልተናገሩትን የምታሰብ ከሆነ የሰዎችን ትክክለኛ ማንነት ልትደርስበት ትችላለህ፡፡ ብዙ ሰዎች ከሚናገሩት በታች አልያም ከሚናገሩት በላይ ናቸው፡፡ የተናገሩትን እሱኑ በትክክል የሆኑ ማግኘት ከባድ ነው፡፡ ወይ ይጨምራሉ፤ ወይ ይቀንሳሉ፤ አልያም ያልሆኑትን ለመምሰል ይሞክራሉ፡፡
ታዋቂዋ አሜሪካዊ የፊልም ተዋናይት እና የቴሊቭዥን አቅራቢ እንዲሁም ኮሜዲያን የሆነችው ኤለን ዴጄነሬስ (Ellen Degeneres) ‹‹ሰዎች የማያዩትን አያለሁ፤ ሰዎች ትኩረት ያላደረጉበትን፣ ያልተረዱትንና ዋጋ ያልሰጡትን ለመረዳት እጥራለሁ፡፡ ለዚህ ይመስለኛል ኮሜዲያን የሆንኩት፡፡ ሰዎች በሚያዩትና በማያዩት መካከል ትንሽ ቦታ አለች፡፡ ያቺን ቦታ ነው እኔ የተጠቀምኩባት›› ትላለች፡፡ እውነት ነው! ሰዎች የማያዩትን ማየት፣ የማያስተውሉትን ማስተዋል፣ ትኩረት ያልሰጡበትን ትኩረት መስጠት የተለየ አዲስ ሃሳብ እንድትፈጥር የደርግሃል፡፡
ወዳጄ ሆይ.... ሮማዊው ፈላስፋ ሴኔካ ‹‹እኔ ሰውን በአዕምሮ እንጂ በዓይን አልለይም፡፡ ትክክለኛ ዳኛው እሱ ነውና (I do not distinguish by the eye, but by the mind, which is the proper judge of the man)››› የሚለው ሰውን ልትረዳው የምትችለው በነፍሱ መሆኑን አፅንኦት ሲሰጥ ነው፡፡ ዓይንና ጆሮህ በሚሰጡህ መረጃ ብቻ ታምነህ የሰውን ልኩን ልታውቅ አትችልም፡፡ ከቃሉ ጀርባ ያለው ስሜቱን፣ ለንግግሩ መግፍኤ የሆነው መንፈሱን፤ ለድርጊቱ መነሻ የሆነውን ሃሳቡን ለመረዳት ካልሞከርክ የሰውን ማንነት በቀላሉ አታገኘውም፡፡ ለዚህ ደግሞ ዋናው ዘዴ ራስን ማወቅ ነው፡፡ ለእያንዳንዱ ድርጊትህ መነሻ ሃሳብህንና አመለካከትህን ስታውቅ የአንተነትህን ቦታ ታገኘዋለህ፡፡ ራስህን ማወቅ የምትጀምረውም ለሰዎች ከምታሳየው ፌኩ አንተነትህ ጀርባ እውነተኛው አንተነትህን መረዳት ስትችል ነው፡፡ ከዛ በኋላ ነው ሌሎች ሰዎችን ከንግግራቸውና ከፊታቸው ባሻገር ያለውን ትክክለኛ መልካቸውን አጥርተህ ማየት የምትችለው፡፡
ቸር መረዳት!
ኢትዮጵያና ኢትዮያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
------------------
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ሠኞ ነሐሴ ፳ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም.
ምህዋረ ሃሳብ
“የህይወትህ ጉዳይ ያለው ካለፈው ይልቅ የሚቀጥለው ላይ ነው”
Prescribe versus Subscribe
ጸሐፊ፦እሸቱ ብሩ ይትባረክ
አቅራቢ፦ተስፋዬ ማሞ
ብልሆች ትዕግስተኞች ናቸው፤ ሞኞች ጠባቂዎች ናቸው!
(Patience is not the ability to wait)
(እ.ብ.ይ.)
ብልሆች ትዕግስተኞች ናቸው፤ ሞኞች ጠባቂዎች ናቸው፡፡ ጠባቂነት ትዕግስተኝነት አይደለም፤ ትዕግስትም ጠባቂነት አይደለም፡፡ የምትታገሰው እየሰራህ ነው፤ ግብህን ቆመህ አይደለም የምትጠብቀው፤ እየሄድክ ነው የምትደርስበት፡፡ መጠበቅ በሽታ ነው፡፡ ከመጠበቅ በሽታ መዳን የሚቻለው በስራ ነው፡፡ ከሰው የምትጠብቅ ከሆነ መተማመኛህ ውጫዊ ነገር ነው፡፡ ከጊዜ የምትጠብቅም ከሆነ ጊዜ በራሱ ይዞት የሚመጣው ነገር የለም፡፡ በጊዜ ውስጥ ያለኸው አንተ ነህ አምጪውም አስቀሪውም፡፡ ዕድል የሚሰምርልህ፣ አጋጣሚ የሚሳካልህ እጅና እግርህን ታቅፈህ ቁጭ ብለህ በመጠበቅ ሳይሆን የልብህን በር ለመልካም አጋጣሚ ክፍት ስታደርግና ዕድልህን ፍለጋ አደባባይ ስትወጣ ነው፡፡ ሎተሪ ካልቆረጥክ እንደማይደርስህ ሁሉ ልታገኘውን የምትሻውን ዝም ብለህ ከጠበቅከው አይመጣም፤ ከሞከርከው ግን አንተው ራስህ በጊዜ ሂደት ታመጣዋለህ፡፡
በአንድ ሐገር ውስጥ ታማኝ ውሻ የነበረው አልቃድር የሚባል ሰው ነበር፡፡ ይህ ሰው ኑሮ አልሰምርለት ሲል የመከራ ጎጆውን ዘግቶ ላይመለስ ተሰደደ፡፡ ውሻው ለሣምንታት በቤቱ በራፍ ላይ ኩርምት ብሎ ጌታውን ሲጠብቅ ከሰነበተ በኋላ በተኛበት ሞቶ ተገኘ፡፡ የአልቃድርን ውሻ መጨረሻ የተመለከተና ሕይወት የከፋችበት የመንደሩ ነዋሪ፡-
‹‹እሄዳለሁ እንጂ፤ እሄዳለሁ የትም፣
እንደአልቃድር ውሻ ስጠብቅ አልሞትም፡፡››..... ሲል አንጎራጎረ ይባላል፡፡
አዎ ትዕግስት እጅን አጣጥፎ መጠበቅ አይደለም፡፡ ትዕግስተኞች እየሞከሩ፣ እየተፍጨረጨሩ ነው የሚሹትን የሚጠብቁት፡፡ ትዕግስት የመጠበቅ ችሎታ አይደለም፡፡ ይልቁንስ እቅድን በትናንሽ ጊዜ ከፋፍሎ በትንሹ እያሳኩ ትልቁን ግብ ለማሳካት ጠንክሮ የመስራት ችሎታ ነው፡፡
ብዙዎቻችን የምንወደውንና የምንፈልገውን ነገር ያላገኘነው ነገርየውን ስለምንጠብቀው ብቻ ነው፡፡ አብዛኛዎቻችን ከቤተሰብ እንጠብቃለን፤ ከወዳጆቻችን እንጠብቃለን፤ ከአለቃችን እንጠብቃለን፤ ከመንግስት እንጠብቃለን፤ ከጊዜ እንጠብቃለን፤ ከአምላክ እንጠብቃለን፡፡ ጠባቂነት ተጠናውቶናል፡፡ ፍቅርንም፣ ደግነትንም፣ ቅን አሳቢነትንም፣ ሰላምንም የምንጠብቀው ከሌላ ነው፡፡ ምንም ነገር እንዲሰጠን (ጠብቆ ይነበብ) እንጂ እኛ ለመስጠት ፍቃደኛ አይደለንም፡፡ እኛ የምንፈልገውን ሌላውም እንደሚያስፈልገውም አንረዳም፡፡ ማህተመ ጋንዲ ‹‹ትዕግስት ማጣት በጦርነቱ መሸነፍ ነው (To lose patience is to lose battle)›› የሚሉን ለዚህ ነው፡፡ አላማህን የሚያደነቃቅፍ ሳንካ ሲገጥምህ ትዕግስት የምታጣ ከሆነ የኑሮህን ጦርነት እየተሸነፍክ ነው ማለታቸው ነው፡፡ እየተንገዳገዱ መራመድ፣ እየወደቁ መነሳት የሚቻለው ትዕግስት ሲኖር ነው፡፡ ትዕግስተኞች ከልፋታቸው የሚጠብቁ፤ ዘርተው ለማጨድ ግባቸውን እየተንከባከቡ፣ እቅዳቸውን ውሃ እያጠጡ ፍሬውን በተስፋ የሚጠባበቁ ምርጥ ገበሬዎች ናቸው፤ ጠባቂዎች ግን እንዲሁ በነፃ ከሰማይ መና የሚጠብቁ አደገኛ ቦዘኔዎች ናቸው፡፡
ወዳጄ ሆይ... መጠበቅ በራስ የሕይወት ጊዜ ላይ መተኛት ነው፡፡ የተኛ ከሞተ የሚሻለው መንቃት ስለሚችል ነው፡፡ አሁን ካልነቃህ፣ ዛሬ ራስህን ካልቀሰቀስክ የመኝታ ዘመንህ ይረዝማል፡፡ የመንቂያ ጊዜ አሁን ነው፡፡ ትክክለኛውን የለውጥ ጊዜ የምትጠብቅበት ትክክለኛው ሰዓት ነገ ሳይሆን ዛሬ ነው፡፡ አሁን የነገ አልፎም ተርፎም የወደፊቱ የሕይወትህ ዕጣ ፋንታ መክፈቻ ቁልፍ ነው፡፡ ስለነገ እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ ስለወደፊቱ ለማወቅ አይቻልም፡፡ ነገ ጉልበት ሊከዳህ ይችላል፡፡ ከነገ ወዲያ በህይወትህ ላይ ምን እንደሚፈጠር የማወቅ ችሎታ የለህም፡፡ በእጅህ ያለው ውዱ ሀብትህ አሁን ነው፡፡ ነገን አትጠብቅ፡፡ ዛሬህን ተንከባክበህ ያዘውና ተጠቀምበት፡፡ ዛሬን በእጃቸው ያደረጉ ነገም፣ ወደፊትም የነሱ ነው፡፡ እየሰሩ መታገስ እንጂ ባዶ እጅ ሆኖ መጠበቅ የትም አያደርስህም፡፡ አርባአራት ነጥብ!
ቸር ትዕግስት! ደግ ጅማሬ!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
-----------------------------------
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
ማግሠኞ ነሐሴ ፯ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም.
‹‹ፊት አቃጣሪ ነው፤ በጓዳ የሸሸግከውን በአደባባይ ያወጣዋል!››
(እ.ብ.ይ.)
ፊት ላይ የተፃፈ፤ በግምባር የተከተበ ብዙ ድብቅ ፅሁፍ አለ፡፡ ፅሁፉ የስሜት ዓይነትን፣ የጀርባ ማንነትን፣ አሁናዊ ሁኔታን ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ነው፡፡ ግምባር መረጃ ሰጪ ነው፡፡ መልክ የትውስታ ማህደራችን ውስጥ ይቀመጣል፡፡ የአንድን ሰው ማንነት ስናስታውስ ቀድሞ የሚመጣልን ፊቱ ነው፡፡ በመቀጠልም አነጋገሩ፣ አካሄዱ፣ አሳሳቁ፣አስተሳሰቡ፣ ሁኔታው ሁሉ ይከተላል፡፡ ፊት ቀዳሚ ነው፡፡ ፊት ሲኮሳተር፣ ፊት ሲጨማደድ፣ ፊት ሲከሳና ሲጠቁር፣ ፊት ሲፈካና ሲበራ፣ ፊት ሲያብረቀርቅ የሰውየውን ውስጣዊ ሁኔታ ያሳብቃል፡፡ ፊት አቃጣሪ ነው በጓዳ የሸሸግከውን በአደባባይ ያወጣዋል፡፡ የዓኖችህ መንቀዥቀዥ የፊትህ መገርጣት አለመረጋጋትህንና ምቾት የነሳህ ነገር እንዳለ ያስረዳል፡፡ ንጉስ ሠለሞን ‹‹ጋለሞታ ሴት በዓይኗ ታስታውቃለች›› እንዲል የዓይንና የፊት ቅንብር የትየለሌ መረጃ ይሰጣል፡፡ ፊታችን የእኛነታችን ማሳያ ስክሪን ነው፡፡ አፎች ብቻ ሳይሆኑ ፊቶችም ይናገራሉ፡፡ መፅሐፍ ብቻ ሳይሆን ግንባርም ይነበባል፡፡
በርግጥ ፊት ሁሉንም በዝርዝር አያሳይም፡፡ የፊቱ ባለቤት የፊቱን ሁኔታ የሚቆጣጠር ከሆነ የተመልካቹን እይታ ሊያዛባው ይችላል፡፡ ፊት የሚያሳየው እንዳለው ሁሉ የሚደብቀውም አለው፡፡ ድፍኑ እንጂ ዝርዝሩ ሁሉ በ’”ፊት አይታይም፡፡ የሳቀ የሚመስል ፊት ሁሌ ሳቂታ ነው ማለት አይደለም፡፡ ያዘነም የሚመስል ፊት ሁሌም ያዘነ ነው ማለት አይቻልም፡፡ ጥርስ ቢገጥጥም ፊት ላይስቅ ይችላል፡፡ አንዳንድ ፊት ተመልካቹን ሊያሳስት ይችላል፡፡ ጥቂት ፊት በተፈጥሮው ሰውየው ያልሆነውን ያንፀባርቃል፡፡ የተከፋ የሚመስል ነገር ግን ያልተከፋ፤ ክፉና ጨካኝ የሚመስል ነገር ግን ሩህሩህ የሆነ፤ የተደሰተ የሚመስል ነገር ግን ያልተደሰተ ብዙ ፊት አለ፡፡ ፊት አንድም የሆድን ያሳብቃል፤ አንድም የውስጥን ይደብቃል፤ አንድም ተፈጥሮን ይገልጣል፡፡ ፊትን መተንተን መቻል ትልቅ ጥበብ ይጠይቃል፡፡
ፊት ትንሽ ቢመስልም የመላ አካላችን ወኪል ነው፡፡ ሰዎች ቁርጭምጭሚታችንን አያስታውሱትም፤ አውራ ጣታችን ምን እንደሚመሰል ትኩረት አይሰጡም፤ ፊታችንን ግን በደንብ ይለዩታል፡፡ ፈጣሪ በስምንት ቢሊየን ሰዎች ፊት ላይ የተለያየ መልክ ስሎበታል፡፡ የእግዚአብሔር ስራ ግሩም ነው፡፡ የሰው ስራ ቢሆን ግን የስንቱ ፊት በተደጋገመና አንድ ዓይነት በሆነ ነበር፡፡ በመንታዎች እንኳን አምላክ የተለያየ የፊት ስዕል አስቀምጧል፡፡ አይደንቅም!? ፊት አንድም ፈጣሪ የሳለው ተንቀሳቃሽ ስዕል ነው፤ አንድም በስሜት ውጣውረድ እኛ ራሳችን በራሳችን ላይ የምንስለው የራሳችን ምስል ነው፡፡ ዊሊያም ሼክስፔር ‹‹እግዚአብሔር የሰጠህ አንድ ፊት ነው፡፡ አንተ ግን ሌላ ፊት አድርገኸዋል፡፡ (God has given you one face, and you make yourself another)›› የሚለው ለዚህ ነው፡፡ እውነተኛውን የሰውነት መልካችንን በኑሯችን፣ በአስተሳሰባችን የለወጥን እልፍ ነን፡፡
የሰው ፊት እሳት ነው፤ በቸገረህ ጊዜና በተዋረድክ ጊዜ ይገርፍሃል፡፡ የቸገረው ሰው ችግሩ አደባባይ ሲያወጣው የሰው ፊት ማየት ያስፈራዋል፡፡ ሌባ እጅ ከፍንጅ ሲያዝ መጀመሪያ የሚያስጨንቀው እስር ቤት መግባቱ ሳይሆን የሰው ፊት ማየቱ ነው፡፡ ፊት የክብርህና የሰውነትህ መገለጫ ነው፡፡ ፊት ሲነሱህ የምትበሽቀው፤ ፊታቸውን ሲያጨማድዱብህ የምትበግነው፣ ፊት ሲሰጡህ የምትደሰተው የፊት ሚስጥር ከሞራል፣ ከክብርና ከስብዕና ጋር የተገናኘ ስለሆነ ነው፡፡ አንዳንድ ሰው ቀለብ ይቆርጥልህ ይመስል ምንም ሳታደርገው በፊቱ ይገላምጥሃል፡፡ ግልምጫ፣ ኮስታራነት ሰዎች ጥላቻቸውን የሚገልጹበት የፊት መሳሪያ ነው፡፡ ፊታቸውን በማየት ብቻ ሰዎች ላንተ የሚሰጡትን ቦታ ማወቅ ትችላለህ፡፡
ፊት ብቻውን በራሱ ብዙ መናገር ይችላል፡፡ የአፍና የዓይን እንቅስቃሴ ሲጨመር ደግሞ የፊት መረጃ የተሟላ ይሆናል፡፡ ዓይንና ፊት ሲግባቡ ለተመልካቹ የማያሳስት መረጃ ይሰጣሉ፡፡ አፍ ቢንቀዠቀዥ እንኳን ዓይንና ፊት ከተናበቡ ተመልካቹ በ’አፍ ከቀረበለት መረጃ ይልቅ ከ’ፊት ያገኘውን ያስቀድማል፡፡ አዳም ረታ ‹‹አፍ›› በተባለ መፅሐፉ ገፅ 149 ላይ ‹‹አፍ ምግብ ማስገቢያ ብቻ ሳይሆን የፊትን ቅጥ እንደሚያበጅ የገባኝ ያኔ ነው›› ያለው የፊት ውበት የአፍ፣ የዓይን፣ የፀጉር፣ የአፍንጫና የጆሮ ቅንብር ውጤት መሆኑንም ለማስገንዘብ ነው፡፡
ፕሮፌሰር ጄሮድ ፓሮት (Professor Gerrod Parrott) የተባለ የስነ-አዕምሮ ተመራማሪ የሰው ልጅ 134 ዓይነት ስሜቶች አሉት ይለናል፡፡ ከነዚህ ውስጥ ዋና ዋና የሚባሉት መውደድ፣ መደሰት፣ ማዘን፣ መፍራት፣ መናደድና መደነቅ ናቸው፡፡ ሌሎቹ እንደጥርጣሬ፣ ቁጭት፣ ፀፀት ወዘተ የመሳሰሉት በነዚህ ስር የሚገኙ ናቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ታዲያ በመልክ የሚገለጡት ፊት ላይ ነው:: ሌላኛው የመስኩ ተመራማሪ ፕሮፌሰር አልበርት መህራቢያን (Albert Mehrabian) ደግሞ የሰው ለሰው የስሜት ግንኙነት የሚካሄደው ሰባት በመቶ በሚናገራቸው ቃላት፣ 38 በመቶ በድምጽ አወጣጡ፣ 55 በመቶ ደግሞ በአካል እንቅስቃሴውና በፊቱ እንደሆነ በጥናቱ አረጋግጧል፡፡ ፊት ከቋንቋም በላይ ነው የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ጥሩ አስተዋይ አንባቢ ወይም ልባም ተመልካች ከተገኘ እነዚህን ስሜቶች ከሰው ግንባር ላይ በቀላሉ ማንበብ ይችላል፡፡
ወዳጄ ሆይ... እንግሊዛዊው ቲያትረኛ ጀምስ ኤሊስ ‹‹ከአስቀያሚ አዕምሮ መልከ-ጥፉ ፊት ይሻላል (Better an ugly face than an ugly mind)›› እንዲል ህሊናህን ፉንጋ አታድርገው፡፡ ከሰው ጋር ለመኖር ብለህ ባለመንታ ፊት (Two-Faced) አትሁን፡፡ ለአንዱ ሌላ ፊት ለሌላው ሌላ ፊት የሚያሳዩ ሰዎች በራሳቸው የማይተማመኑና አቋም የሌላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ ካህሊል ጂብራንም ‹‹ውበት በፊት ላይ ሳይሆን በልብ ውስጥ የሚገኝ ብርሃን ነው (Beauty is not in the face; Beauty is a light in the heart)›› የሚልህ ፊትህን የሚያፈካው ውስጣዊ አንተነትህ እንጂ የምትቀባባው ኮስሞቲክ አይደለም ለማለት ነው፡፡ ቆዳን መንከባከብ ደግ ነገር ነው፤ ነገር ግን ልብን፣ አዕምሮንና ውስጣዊ ሰላምን ከመንከባከብ በላይ አይሆንም፡፡ በቋሚነት የፊትህን ውበት የሚጠብቀው የሃሳብህ ቅባት ነው፡፡ በመልካም አስተሳሰብና በበጎ ስራ የወዛ ልብ ግንባርህንም ያስውባል፡፡
ከልብ ጋር የተስማማ ፊት!
ቸር ፊት! ደግ ፊት!
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘላለም ይኑሩ!
----------------------------------
እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.)
እሁድ ሠኔ ፪ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም.
Welcome To Amharic films Best Place To find Amharic Movies
አዳዲስ እና የድሮ አማርኛ ፊልሞችን እና አማርኛ ተከታታይ ድራማዎችን ለማግኝት ቻናላችንን Join ይበሉ ።
Share:- @Amharic_Films
ለማስታወቂያ - @Abusheymc & @Alpha6249
Buy ads: https://telega.io/c/Amharic_films
Last updated 1 year, 8 months ago
ስለ መድፈኞቹ የሚወጡ መረጃዎች ለማግኘት የትም መሄድ አያስፈልግም
- የዝዉዉር ዜና
- የአሰልጣኞች አስተያየት
- የተጨዋቾች የህይወት ታሪክ
- ጨዋታዎችን በቀጥታ ስርጭት
ለማስታወቂያ ስራ --> @Aymu_xo
Last updated 3 weeks, 1 day ago
╔╦╦═╦╔╦═╦═╦═╗
║ እንኳን ደህና መጡ | |
╚══╩═╩═╩╩╩╩═╝
➟ እንኳን ወደ ትልቁ የሊቨርፑል ( መርሲሳይድ) ቻናል በደህና መጡ ።
◉ ስለ ሊቨርፑል ◉
? ዝውውሮች
? ውጤቶች
? የጨዋታ ፕሮግራሞች
? እንዲሁም የተጨዋቾች ግለ ታሪክ
? ጨዋታዎችን በቀጥታ ወደናንተ የምናደርስ ይሆናል።
Owner:- @hackersolo0⭐️
Last updated 2 months, 2 weeks ago