ስንክሳር ዘተዋሕዶ

Description
የየዕለቱ ስንክሳር ይቀርብበታል
Advertising
We recommend to visit

★ሰውን በማዝናናት የብቃት ማረጋገጫ ያለው ብቸኛው ቻናል ሁሌም Telegram ላይ በጥበብ ደምቀን እናሸበርቃለን

💌 Contact us, @Modenyazbot

»የተመረጡ እና ማንም ያላያቸው የአማሪኛ ቀልዶች እንዲሁም የሚያስደንቁ ስዕሎችንና ቪዲዮ ያገኛሉ።

° ° [ ሙድ እንያዝ በእኛ የአራዶች መዝናኛ ] ° °

° ° Creator @Teke_Man ° °

Last updated 2 weeks ago

☕ ስለ ኢትዮጲያ ቡና የሚወጡ ወቅታዊና ትክክለኛ የክለቡ መረጃዎች አዚህ ያገኛሉ!

➪የዝዉዉር ዜና
☞የአሰልጣኞች አስተያየት
➪ጎሎች እና ቪዲዮዎች
☞የተጨዋቾች የህይወት ታሪክ
➪ጨዋታዎችን በቀጥታ ስርጭት ከየስታድየሙ !

➡መወያያ ግሩፓችን @Ethiopia_coffee_Sc

📩ሀሳብ ወይም አስተያየት ካሎት
በዚህ 👉 @EthiopianCoffeeScBot ✍
BOT ማድረስ ይችላሉ!

Last updated 2 weeks, 1 day ago

እንኳን ወደ # ሉሲ የቴሌግራም ቻናል በደህና መጡ
#የሉሲ /LUCY DINKINESH E/ቤተሰብ ሰለሆኑ ደስብሎናል።

መረጃ መስጠት የምትፈልጉ በዚ አድርሱን 👉 @CACA77

# የኢትዬጵያዊነት የአሸናፊነት መገለጫ አርማችን ነው!
ነፃነታችንን 💪በፈርጣማው ጡንቻችን ይረጋገጣል
👉 ኢትዬጵያዊነት አርበኝነት የማንነት አርማች ነው
🙏🙏🙏

Last updated 1 month, 3 weeks ago

3 months, 3 weeks ago

ከዚህም በኋላ መኰንኑ እለእስክንድሮስ ቂርቆስንና እናቱን ወደ አደባባይ ያመጡአቸው ዘንድ አዘዘ ያን ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ ነበርና እንዲህም አለ ሕፃኑንና እናቱን ከቆዳቸው ጋር ራሳቸውን ላጩአቸውና በላያቸው የእሳት ፍሞችን ጨምሩ እርር ብለው እንዲቃጠሉ ዳግመኛም አራት ችንካሮችን ከትከሻዎቹ እስከ ተረከዙ ድረስ እንዲተክሉበት አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ መጥቶ ሥቃዮችን ከርሱ አራቀ።

ዳግመኛም ከጥዋት እስከ ማታ ከሥቃይ መሣሪያዎች ውስጥ ጨምረው አዋሏቸው ግን ማሠቃየት ተሳናቸው። ከዚህም በኋላ ከማምጠቂያው ውስጥ ጨምረው መገዙአቸውና አመድ እስከሆኑ ከቅባትና ከጨው ጋር በብረት ምጣድ ውስጥ ቆሉአቸው ጌታችንም ከሞት አስነሥቶ አዳናቸው።

ወደ መኰንኑም በገቡ ጊዜ እንዲህ አላቸው በእውነት ከሙታን ተለይታችሁ የተነሣችሁ ከሆነ ይህ ጫማዬ ከእግሬ ወጥቶ እንደ ቀድሞው ሕያው እንዲሆን አድርጉ ሕፃን ቂርቆስም በጸለየ ጊዜ ያ ጫማ ታለቅ በሬ ሆነ ከአንገቱም ፍየል ወጣ።

በዚያንም ሰዓት ለዐሥራ አንድ ሽህ አራት ሰዎች በሬውንና ፍየሉን አርደው ምሳ እንዲያደርጉላቸው መኰንኑ አዘዘ እንዲህም አለ ይህ በቅቷቸው ከጠገቡ ከዚህም ሌላ ምግብ ካልፈለጉ የተሠራው ሁሉ ዕውነተኛ ነዋሪ ነው። ከዚህም በኋላ አርደው ምሳ አደረጉላቸውና ከፍየሉ ሥጋ ስድስት እንቅብ ከበሬው ሥጋ አራት እንቅብ አተረፉ መኰንኑም የተረፈውን ሥጋ አይቶ ወደ ባሕር እንዲጥሉት አዘዘ።

መኰንኑም ቢያፍር የሕፃኑን ምላስ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ጌታችንም ምላሱን መለሰለት ዳግመኛም በታላቅ ጋን ውኃ እፍልተው ሕፃን ቂርቆስንና እናቱን ኢየሉጣን ይጨምሩአቸው ዘንድ አዘዘ እናቱም አይታ ፈረች። ልጅዋም ወደ እግዚአብሔር በጸለየላት ጊዜ አምላካዊ ኃይልን አሳደረባትና ከልጅዋ ጋር ወደ ጋኑ ገባች። እንደ ውርጭም ቀዝቀዛ ሆነ ደግሞም በውስጡ መንኰራኲር ወዳለበት የብረት ምጣድ እንዲጨምሩአቸውና ሥጋቸው እሰከሚቦጫጨቅ እንዲስቡአቸው አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ በሕይወት አወጣቸው።

መኰንኑም እነርሱን ማሸነፍ በተሳነው ጌዜ ቸብቸቧቸውን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ በዚያን ጊዜ ለስም አጠራሩ ስግደት የሚገባው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወረደ ሕፃን ቂርቆስንም የምትሻውን ለምነኝ አለው።

ሕፃኑም ሥጋዬ በምድር አይቀበር ስሜን ለሚጠራ መታሰቢያዬን ለሚያደርግ ቤተ ክርስቲያኔን ለሚሠራ የተጋድሎዬን መጽሐፍ ለሚጽፍና ለሚያጽፍ ወይም ለሚያነበው ለቤተ ክርስቲያኔ መባ ለሚያገባ በውስጧም ለሚጸልይ ለሁሉም ፍላጎታቸውን ስጣቸው ኃጢአታቸውንም ይቅር በል ስሜም በሚጠራበት በዚያች ቦታ የከብት ዕልቂት አይምጣ በሰውም ላይ እባር ቸነፈር በእህልም ላይ ድርቅ የውኃም ማነስ አይሁን።

መድኃኒታችንም የለመንከኝን ሁሉ እሰጥሃለሁ አንተም በቀኜ ትኖራለህ ሥጋህንም ኤልያስ በዐረገበት ሠረገላ ውስጥ አኖራለሁ አለው ሕፃን ቂርቆስም በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት ጌታችንን አመሰገነው። ከዚህም በኋላ በሌሊቱ እኩሌታም ከእናቱ ጋር አንገቱን ተቆረጠ መድኃኒታችንም በማይጠፋ አክሊል ጋረደው ነፍሶቻቸውንም በታላቅ ክብር ከእርሱ ጋር አሳደገ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አብድዩ_ነቢይ

በዚህች ቀን ዕውነተኛ ነብይ አብድዩ አረፈ። ይህም ነብይ የሐናንያ ልጅ ነው። በንጉሥ ኢዮሳፍጥም ዘመን ትንቢት ተናገረ እግዚአብሔርም ስለ ትንሣኤና ስለ ፍርድ ቀን በቃሉ ነገረው።

ሁለተኛም ከእስራኤል ልጆች የሚሆነውን ከአሕዛብም ለቀሩት አጸናቸው አብዝቶ መከራቸውም ገሠጻቸውም። ይህም ንጉሥ አካዝያስ ይጠሩት ዘንድ ወደ ኤልያስ ከላካቸው ሦስተኛ መስፍን ነው። ከእርሱ አስቀድመው የመጡ እነዚያን ሁለት መስፍኖች በኤልያስ ቃል እሳት ከሰማይ ወርዳ ከእነርሳቸው ጋር ካሉ ወታደሮች ጋር በላቻቸው።

ይህ ግን ወደ ኤልያስ በመጣ ጊዜ በፊቱ ተንበርክኮ ሰግዶ ተገዛለት እንዲህም አለው የእግዚአብሔር ሰው ተገዛሁልህ የእሊህ የባሮችህ ሰውነትና የኔ ሰውነት በፊትህ ትክበር በእግዚአብሔር ነቢይ ላይ ፈጽሞ አልታበየምና ነቢዩ ኤልያስም ራራለት ወርዶም ከርሱ ጋር ወደ ንጉሡ ሔደ።

ይህም አብድዩ ከምድራዊ ንጉሥ አገልግሎት የኤልያስ አገልገሎት እንደምትበልጥ የኤልያስም አገልገሎት ለሰማያዊ ንጉሥ አገልገሎት ታደርሳለችና ይህን በልቡ ዐወቀ ስለዚህ ምድራውያን ነገሥታትን ማገልገል ትቶ ነቢይ ኤልያስን ተከተሎ አገለገለው በላዩም ከእግዚአብሔር ሀብተ ትንቢት አደረበትና ትንቢትን የሚናገር ሆነ የትንቢቱም ወራት ሃያ ዓመት ነው ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በዘጠኝ መቶ ዓመት በሰላም በፍቅር አንድነትም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ጎርጎርዮስ_ዘኑሲስ

በዚህችም ቀን ዳግመኛ በሶርያ አገር ያሉ የክርስቲያን ወገኖች የቅዱስ ጎርጎርዮስን የዕረፍቱን መታሰቢያ በዓል ያከብራሉ። ይህም አባት በነፍስ በሥጋ በበጎ ሥራ ሁሉ ከወላጆቹ ጋር ፍጹም ነው። እርሱ እግዚአብሔርን መፍራትንና ትምህርቶችን ተምሮ ዐውቋልና የቋንቋም ትምህርት እጅግ የሚያውቅ የዮናናውያንንም ቋንቋ የሚያነብና የሚተረጒም ለቀና ሃይማኖትም የሚቀና ሆነ በውስጡም በጎ ሥራ በጎ ጠባይ ተፈጸመለት ኑሲስ በምትባል አገርም ላይ ሳይወድ በግድ መርጠው ኤጲስቆጶስነት ሾሙት እርሷም ደሴት ናት የእግዚአብሔርንም መንጋዎች ጠበቀ በትምህርቱና በድርሰቶቹም ልቡናቸውን ብሩህ አደረገ የብሉያትንና የሐዲሳትንም መጻሕፍት ተረጐመ።

ጳጳስ ሁኖ ስለነበረው ስለ ከሀዲው መቅዶንዮስ በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ዘመን በቊስጥንጥንያ ከተማ የመቶ ሃምሳ ኤጲስቆጶሳት የአንድነት ስብሰባ በሆነ ጊዜ ይህ ጎርጎርዮስ ከአባቶች ኤጲስቆጶሳት ጋር ሁኖ የሰባልዮስን ወገኖች መቅዶንዮስንና አቡሊናርዮስን ተከራከራቸው መልስ አሳጥቶም አሳፈራቸው። ስሕተታቸውንም ገለጠ። ይህም የካቲት አንድ ቀን ተጽፎአል የእነዚህንም ክህደት አስወገደ በቃሉ ሰይፍነትም የንባባቸውን የስሕተት ሐረግ ቆራርጦ አጠፋ ከተሰበሰቡትም ጋር በሰላም ተመለሰ እነርሱ በድል አድራጊነት እነዚያም ከሀ**ድያን በኀፍረት ሆነው ተመለሱ ።

ወደ መልካም እርጅና ደርሶ እግዚአብሔርንም ደስ አሰኝቶ አገልገሎ በሰላም አረፈ እነሆ በዚህ ወር ጥር ሃያ አንድ ቀን ከገድሉ ጥቂት ጽፈናል ይኸውም በግብጻውያን ዕረፍቱ ነው።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር)

3 months, 3 weeks ago

#ጥር_15

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር ዐሥራ አምስት በዚህች ዕለት የከበረ ሕፃን #ቅዱስ_ቂርቆስና_ቅድስት_ኢየሉጣ በሰማዕትነት አረፉ፣ #ነብዩ_ቅዱስ_አብድዩ አረፈ፣ በሶርያ ክርስቲያን ወገኖች #የቅዱስ_ጎርጎርዮስን የዕረፍቱን መታሰቢያ በዓል ያከብራሉ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ቂርቆስና_እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ

ጥር ዐሥራ አምስት በዚህች ዕለት የከበረ ሕፃን ቂርቆስ እናቱ ብፅዕት ኢየሉጣ ዳግመኛ ለከበረ ሕፃን ቂርቆስ ማኅበር የሆኑ ዐሥራ አንድ ሺህ አራት ሰዎች በሰማዕትነት ሞቱ።

በዚያንም ወራት የክብር ባለቤት የሆነ ክርስቶስን በሚያምኑ የክርስቲያን ወገኖች ላይ ታላቅ መከራና ስደት ሆነ። ስሟ ኢየሉጣ የሚባል አንዲት ሴት ነበረች እርሷም ከታናሽነቷ ጀምራ ደግ ናት ስደትም እንደሆነ በሰማች ጊዜ መኰንኑን ከመፍራት የተነሣ ሕፃኗን ይዛ ከሮም ከተማ ተሰዳ የኪልቅያ አውራጃ ከሆነ ከጠርሴስ ደርሳ ከዚያም በሀገሮች ውስጥ እየተዘዋወረች ተቀመጠች።

ወደዚያች አገርም ያ ከእርሱ የሸሸችው መኰንን እለእስክንድሮስ መጣ ጭፍሮቹም ክርስቲያኖችን ፈለጓቸው። ይቺንም ቅድስት ኢየሉጣን አግኝተው ያዝዋትና ወደ መኰንኑ አደረሷት የክርስቲያን ወገንም እንደሆነች ነገሩት።

መኰንኑም ሴትዮ ተናገሪ ከወዴት ሕዝብ ወገን ነሽ ነገድሽ ምንድን ነው ሀገርሽስ ወዴት ነው አላት። የከበረች ኢየሉጣም እንዲህ ብላ መለሰችለት የአንጌቤን ሰው ለሆንኩ ለእኔ ወገኖቼ ለኢቆንዮን አገር አለቆች የሆኑ ኤሳውሮሳውያን ናቸው እኔም በአንተ ምክንያት ሸሽቼ ነበር እነሆ ዛሬ ግን በእጅህ ውስጥ ነኝ አለችው።

መኰንኑም በእጄ ውስጥ እንደተገኘሽ ታውቂያለሽን አላት አሁንም የሚሻልሽን ምረጪ ስምሽንም ተናገሪ እኔንም እሺ በይኝና ለአማልክት ሠዊ የከበረች ኢየሉጣም ለረከሱ አማልክት እኔ አልሰዋም አለችው መኰንኑም ስምሽን ስጪ ተናገሪ አላት እርሷም የኔ ስም ክርስቲያን መባል ነው አለችው። መኰንኑም ይህስ ስንፍና ነው የሚጠቅምሽ አይደለም እንዳትሞቺ ስምሽን ስጪ ተናገሪ አላት። የከበረች ኢየሉጣም የኔ ስም ክርስቲያን መባል እንደሆነ ነገርኩህ ሞት የሚሽረው በሰዎች ዘንድ የምጠራበትን ከፈለግህ ስሜ ኢየሉጣ ነው ብላ መለሰችለት።

መኰንኑም ጽኑ የሆኑ ሥቃዮችን በላይሽ ሳይመጣ ተነሥተሽ መሥዋዕትን ለአማልክት አቅርቢ አላት። የከበረች ኢየሉጣም ዕወነት ነገርን ለመሥራት የምትሻ ከሆነ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነ ሕፃን ልጅ ይፈልጉ ዘንድ ወደ ሀገሩ መንደር ላክ ወዳንተም ያምጡትና የምንገዛለትንና የምናመልከውን እርሱ ይንገረን አለችው።

ያን ጊዜም የሦስት ዓመት ልጅ ይፈልጉ ዘንድ መኰንኑ ወታደሮችን ላከ የሀገር ሰዎችም ልጆቻቸውን ሠውረዋልና አላገኙም ከዚያም ከከተማው ቅጽር ውጭ በፀሐይ መውጫ ወዳለው በረሀ በኩል ወጡ የቅድስት ኢየሉጣንም ልጅ አገኙት ይህ ሕፃን የስንት ዓመት ልጅ ነው ብለው ስለርሱ ጠየቁ ሰዎችም ይህ ሕፃን የሦስት ዓመት ሲሆን የክርስቲያናዊት መበለት ልጅ ነው አሏቸው።

ያንንም ሕፃን ይዘው ወደ መኰንኑ ወሰዱት መኰንኑም መልኩ የሚያምርና ደም ግባት ያለው እንደሆነ በአየው ጊዜ ደስ የምትል ደስተኛ ሕፃን ሰላምታ ይገባሃል አለው። ሕፃኑም እኔን ደስተኛ ማለትህ መልካም ተናገርክ ላንተ ግን ደስታ የለህም እግዚአብሔር ለዝንጉዎች ደስታ የላቸውም ብሏልና ብሎ መለሰለት መኰንኑም ሕፃኑን ሳልጠይቅህ ይህን ያህል ትመልስልኛለህን አለው። ሕፃኑም ገና ከዚህ የሚበዛ ነገርን እመልስልሃለሁ አለው።

መኰንኑም ሕፃኑን ስምህ ማን ነው አለው ከንጹሕ ዐዘቅትና ከማይለወጥ ከማይጠፋ ውኃ የተገኘ ሕፃን ስሜ ክርስቲያን መባል ነው ብሎ መለሰለት። መኰንኑም ዳግመኛ እንዳትሞት ስምህን ንገረኝ አለው የከበረ ሕፃንም ስሜ ክርስቲያን መባል እንደሆነ ነገርኩህ ሞክሼ ስም የምትሻ ከሆነ እናቴ የሰየመችኝ ቂርቆስ ነው።

መኰንኑም ሕፃን ቂርቆስን እሺ በለኝና ለአማልክት ሠዋ በሥጋህም ስታድግ እሾምሃለሁ በብዙ ወርቅና ብርም አከብርሃለሁ አለው። ሕፃኑም የሰይጣን መልእክተኛ ለዕውነትም ጠላቷ የሆንክ ከእኔ ራቅ አለው።

መኰንኑም ሰምቶ ተቆጣ ደሙ እንደ ውኃ እስከሚፈስ ቆዳውን እንዲጨምቁትና እንዲገፉት አዘዘ። የከበረች ኢየሉጣም የልጅዋን ትዕግሥት ባየች ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰገነችው።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ጨውና ሰናፍጭ አምጡ አለ የሁለቱንም አፍንጮቻቸውን ከፍተው ያንን ጨውና ሰናፍጭ እንዲጨምሩባቸው አዘዘ ያን ጊዜ ሕፃኑ ትእዛዝህ ለጕረሮዬ ጣፋጭ ሆነ ከማርና ከስኳርም ለአፌ ጣመኝ ብሎ ጮኸ።

ሁለተኛም መኰንኑ እንዲህ ብሎ አዘዘ የረዘሙና የተሳሉ በእሳትም እንደ ፍም የጋሉ ዐሥራ አራት የብረት ችንካሮች አምጡ ሰባቱን በእናቱ አካላት ውስጥ ጨምሩ በሕፃኑም ሁለት በጆሮዎቹ ሁለት በዐይኖቹ ሁለት በአፉና በአፍንጫው አንድ በልቡ ጨምሩ እንዲህ ሲጨመርበት ጆሮዎቹ እንዲአሩ ዐይኖቹም ይጠፉ ዘንድ አንደበቱም ይቃጠል ዘንድ ወደ ልቡም ጽኑ ሕማም ገብቶ እርሱ ከዚህ ዓለም በሞት እንዲለይ ለእናቱም እንዲሁ አድርጉ ችንካሮችም በቅዱሳኑ በሥጋቸው ሁሉ ተጨመሩ።

የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ትእዛዝ የብረቶቹ ግለት ጠፍቶ እንደ በረዶ ቀዘቀዘ ጤነኞችም ሆኑ መኰንኑም ወደ ወህኒ ወስዳችሁ በዚያ አሥራችሁ ዝጉባቸው አለ።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ የሥቃይ መሣሪያ ይሠራ ዘንድ አንዳዝዘው ብረትን የሚያቀልጥ ሰው አምጡልኝ አለ። በአመጡለትም ጊዜ ሰይጣኑ ወደ መኰንኑ ልብ ገብቶ አንደበቱን ዘጋውና መናገር ተሳነው ሕፃኑ ፈጥኖ አክሊልን ለመቀበል እንደሚተጋ ሰይጣን ስለ አወቀ ስለዚህ ዘጋው።

ከዚህም በኋላ ሕፃኑ ሠራተኛውን ጠርቶ እኔንና እናቴን የሚያሠቃዩበትን የሥቃይ መሣሪያ መሥራት ትችላለህን ይህ መኰንን ግን ምንም የሚያውቀው ነገር የለም አለው ሠራተኛውም እንደምትሻው በል ንገረኝ እንደምታዝዘኝ እኔ መሥራት እችላለሁ አለው።

ሕፃን ቂርቆስም ሊአዝዝ ጀመረ እንዲህም አለ ሁለት መላጫዎች ስፋታቸው አራት ክንድ የሆነ ለእኔና ለእናቴ ሥራ። ዳግመኛም የሚያስጨንቅ ራስን የሚመታና የሚሰብር አንገትንም የሚያሥር የሚዝቅም ሹካ ዐይንንም የሚያወልቅ አካልንም የሚበሳሳ አፍንጫንም የሚያጣምምና የሚሰብር ጆሮንም የሚልጥ ሕዋሳትን የሚፈታና የሚለያይ እንደ ልጓም ሁኖ ምላስን የሚቆርጥ በሰውነትም ውስጥ ገብቶ የሚንቀሳቀስ ቆላፋ ጉጠትን ጐኖችንም የሚፍቅና የሚቆለምም አስጨናቂ የሆነ ጉልበቶችንና ጭኖችን የሚሰብር ጅማቶችንም የሚቆራርጥ ሥሮችንም የሚመዝ በዚችም አስጨናቂ መሣሪያ ጅማቶችን የሚታታ አድርግ።

ዳግመኛም በላም አምሳል ሰፊ መቀመጫ ከናስ ሥራ ሦስት ቀዳዳዎችንም በዚያ መቀመጫ ውስጥ ቅደድ። በቁመቴም ልክ ሦስት ችንካሮችን ሥራ የችንካሮቹንም ራስ ከናስ አድርገህ በውስጡ ከሚጠሩት ዘንድ ፈጽሞ የማይለይ ልዩ ሦስት ብለህ ጻፍ።

ዳግመኛም ጠምዝዞ ወደ ላይ የሚያወጣ ሁለት መሣሪያ ሁለት መጋዞችን ሁለት የብረት ምጣዶችን ሥራ አሁንም አንድ ታላቅ ጋን ሠርተህ በውስጡ አንገትን የሚጠመዝዝና የሚሠነጥቅ ተሽከርካሪ መሣሪያ አድርግ።

በውስጥ የተሸሸገ የሆድ ዕቃን የሚመረምር እጅን ከብረት ሥራ እኔ የጻዕር ስቃይን የምሠቃይበት ይህ ነው አለ። ብረት ሠሪውም ሰምቶ እጅግ አደነቀ የሚረዱትንም ከሀገር ውስጥ መቶ ሠራተኞችን ሰብስቦ መሥራት ጀመረ በአርባ ቀንም ጨረሰ።

3 months, 4 weeks ago

የከበረ አርኬሌድስም ከመምጣቱ በፊት ለአበምኔቱ መንፈስ ቅዱስ አስረድቶት ነበር ወደርሱም በደረሰ ጊዜ አበ መኔቱ ደስ አለው የከበሩ መነኮሳትን ሁሉንም ሰበሰባቸውና በቅዱስ አርከሌድስ ላይ ፀለዩ። አበ ምኔቱም የምንኩስና ልብስን አስኬማንም አለበሰው መነኮሳቱ ሁሉም በእርሱ ደሰወ አላቸው የእግዚአብሄር ፀጋ በላዩ ተገለፃለችና።

ከዚህም በኃላ የከበረ አርከሌድስ በጠባብ መንገድ ተጠመደ ፅኑ ገድልን ተጋድሏልና ሁልጊዜ በየሰባት ቀን የሚፆም ሆነ በቀንና በሌሊትም ይፀልያል እግዚአብሄርም ሀብተ ፈውስን ሰጥቶት በእምነት ወደርሱ የሚመጡትን ብዙዎች በሽተኞችን አዳነቸው።

የሴቶችንም ፊት ከቶ እንዳያይ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃል ገባ ከእናቱ ዘንድም አስራ ሁለት አመት ያህል ወሬው መሰማቱ በዘገየ ጊዜ በእርሱም የሆነውን አላወቀችም የሞተ መስሏታልና እጅግ አዘነች።

ከዚህም በኃላ የእንግዶችና የመፃተኞች መቀቢያ የሚሆን ቤትን ሰራች መንገደኞችም እንዲአድሩበት አደረገች በአንዲትም እለት የብፁእ አርከሌድስን ዜና ሲናገሩ መንገደኞችን ሰማቻቸው እንርሱም ቅድስናውን ተጋድሎውን ምልክቶቹንም የመልኩንም ደም ግባት ሰምታ ልጅዋ እንደሆነ አወቀች ደሰግመኛም መንገደኞችን ጠየቀቻቸው ስራውን ሁሉ ነገሩዋት እርሱ ህያው እንደሆነ ተረዳች።

በዚያንም ጊዜ ተነስታ ወደ ከበረ ሮማኖስ ገዳም ሄደች ወደ ልጅዋ ወደ አርከሌድስም እንዲህ ብላ ላከች እነሆ ፊትህን አይ ዘንድ ወድጄ እኔ እናትህ መጥቻለሁ። እርሱም ከቶ የሴቶችን ፊት እንዳለሰይ ከክበር ባለቤት ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ቃል ገብቻለሁና ቃል ኪዳኔን ማፍረስ አይቻለኝም ብሎ መልሶ ወደርሷ ላከ ።ዳግመኛም ፊትህን ካላሳየኸኝ እኔ ወደ ዱር እሄዳለሁ አራዊትም ይበሉኛል ብላ ወደርሱ ላከች።

የከበረ አርከሌድስም እርሷ እንደማትተወው እርሱም ለእግዚአብሄር የገባውን ቃል ኪዳን ማፍረስ እንደማይቻለው በአወቀ ጊዜ ነፍሱን እንዲወስዳት ወደ ጌታችን ለመነ ከዚህም በኃላ የበሩን ጠባቂ ወደ እኔ ትገባ ዘንድ እናቴን ተዋት አለው ።በገባችም ጊዜ ሙቶ አገኘችውና በታላቅ ድምፅ በመጮህ አለቀሰች ነፍሷንም ይወስድ ዘንድ ወደ እግዚአብሄር ለመነች ልመናዋንም ተቀብሎ ነፍሷን ወሰደ።

ከዚህም በኃላ ስጋዋን ከልጅዋ ስጋ ለይተው ለብቻዋ ሊቀበሩ ወደዱ ከከበረ አርከሌድስም በድን የእናቴን ስጋ ከስጋዬ አትለዩ በህይወቷ ሳለች ታየኝ ዘንድ ልቧን ደስ አላሰኘሁምና የሚል ቃል ወጣ።ይህንንም ቃል በሰሙ ጊዜ አጅግ አደነቁ እግዚአብሄርንም አመሰገኑት ሁለቱንም በአንድ መቃብር ውስጥ ቀበሩአቸው ጌታችንም ለበሽተኞች ታላቅ ፈውስን ከስጋው ገለጠ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_እምራይስ

በዚህችም እለት የከበረች እምራይስ በሰማእትነት አረፈች። ይቺም ብፅእት በክርስቶስ ሀይማኖት ለፀኑ ለከበሩ አባቶች ልጅ ናት ፈሪሀ እግዚአብሄርንም እየተማረች አደገች።በአንዲትም እለት ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ ስትወርድ ስለ ክርስቶስ የታሰሩ እስረኞችን አየች።

እንርሱም ጳጳሳት ቀሳውስትና ዲያቆናት ናቸው ከእነርሱም ጋር ስሟን ይፅፍ ዘንድ መዘጋቢውን ለመነችው መዘገባትም ወደ ከሀዲውም መኮንን ወደ ቁልቁልያኖስ አቀረባት።እርሱም ለጣኦት ትሰግድ ዘንድ በብዙ ነገር ሸነገላት እምቢ ባለችውም ጊዜ ቸብቸቦዋን ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ከተባባሪዎቿም ጋር ምስክርነቷን ፈፀመች።

አምላከ ቅዱሳን ለቅዱሳኑ ካደለው ፍቅራቸው ለእኛም አይንሳን:: በረከታቸውንም ያብዛልን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር_እና_ጥቅምት)

4 months ago

#ጥር_10

#ጾመ_ገሃድ

ጥር አስር በዚህች ዕለት ምንም ምን መብልን ሰይቀምሱ ምእመናን ሁሉ እስከ ምሽት ይጾሙ ዘንድ ከእኛ አስቀድመው የነበሩ ታላላቅ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን መምህራን ሥርዓትን ሠሩ በምሽትም ቢሆን በታላቁ ጾም ከሚበላው በቀር ጥሉላትን እንዳይቀምሱ። በዚች ዕለት ምእመናን እስከ ምሽት እንደመጾሙን ያዘዙበት ምክንያቱ ይህ ነው የልደትና የጥምቀት በዓል በዓል በረቡዕ ወይም በዓርብ ቀን ቢሆን በበዓለ ኃምሳ የሚበላውን የጥሉላት መብል በጥዋት በመብላት ምእመናን ሁሉ በዓሉን እንዲአከብሩ የከበሩ አባቶቻችን ሐዋርያት አዝዘዋል እሊህ ሁለቱ የእግዚአብሔር ታላላቅ በዓላቶቹ ናቸውና።

እኛ በዚህ በኅላፊው ዓለም ተድላ ደስታ ደስ የሚለን ለሌሎች እንዳይመስላቸው እንደ አይሁድና እንደ አረማውያን በዓል በመብልና በመጠጥ ብቻ እንዳናደርግ ስለዚህ ከልደትና ከጥምቀት በዓል በዋዜማ ያሉትን ሁለቱን ዕለታት እንድንጾም አዘዙን የልደትና የጥምቀት በዓል በረቡዕና በዓርብ ላይ በሚሆን ጊዜ በረቡዕና በዓርብ ፈንታ እንድንጾማቸው ይገባልና በዚህም ሁለት ሥራ ይፈጸምልናል የጾም ሥራና የበዓል ማክበር ሥራ ነው። እንዲሁም በግብፃውያን አብያተ ክርስቲያን የተሠራ ነው።

በይረሙን በእሑድ ወይም በአይሁድ ሰንበት ቀን ቢሆን ይህም ጌታ የተገለጸበት ጥር ዐሥራ ቀን ነው በዋዜማው ዐርብ እስከ ምሽት ይጹሙ አስቀድመን እንደተናገርን ጥሉላት አይብሉ የልደትና የጥምቀት በዓልም ሰኞ ቀን ቢሆን በሰንበት ቀን ይጾም ዘንድ አይቻልም ነገር ግን ጥሉላትን ከመብላት ይጠበቁ።

በጥምቀትም ዕለት ከእኵለ ሌሊት በፊት ተነሥተው በውኃው ላይ ይጸልዩና ይጠመቁ ሕፃናትም በሚጠመቁ ጊዜ በውኃ እንዳይገድፉ ካህናቱም ከመንጋቱ በፊት ቀድሰው ቊርባኑን ያሳርጉ እጅግም ማልደው በጥዋት ከቤተ ክርስቲያን ይውጡ በከበረ ሥርዓታቸው ጌቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙ።

የመለካውያን ወገኖች ግን የልደትና የጥምቀት ዋዜማ በቅዳሜ ቀን ወይም በእሑድ ቀን ቢሆን በሦስት ሰዓት ይቀድሳሉ ከወደዱም የተባረከ ኅብስት ተመግበው ውኃ ይጠጣሉ ከዚህም በኋላ ካህናቱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሁነው በየሰዓቱ በመጸለይ ለበዓሉ የሚገባውን የነቢያትን ትንቢቶች ያነባሉ በዚያች ቀን በምሽት ይኸውም ጥር ዐሥር ነው በውኃው ላይ ይጸልያሉ ይህም አባቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙት አልሆነም። እርሳቸው የኤጲፋንያን በዓል እንዲአክብሩ አዘዋል ይኸውም መድኃኒታችን የተገለጠበት ካኑን በሚባል በሮም ሁለተኛ ወር በሰባት ይህም ጥር ዐሥራ አንድ ቀን ነው።

መለካውያን ግን የከበሩ አባቶች የቤተ ክርስቲያን መምህራን ያዘዙትን ይተላለፋሉ በልደትና በጥምቀት በዓል ዓርብም ረቡዕም ቢሆን አስቀድመው በርሱ ፈንታ ሳይጾሙ በጥዋት ተነሥተው ይበላሉና። እኛንም ከበደላችን ያነጻን ዘንድ በዮርዳኖስም ወንዝ እንደ ተገለጸ የጌትነቱን ክብር በልቡናችን ይገልጥልን ዘንድ የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው።

ጌትነት ክብር ስግደት ለእርሱ ይገባልና ከቸር አባቱ ጋር ይቅር ባይ ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር)

4 months ago

#ጌታችን_ለምን_በሌሊት_ተጠመቀ?
በኃጢአት ጨለማ ስለነበረ ሕዝብ የጽድቅ ብርሃን እንዲወጣለትና በጨለማ የሚመስል ኦሪት ይኖር ስለነበረ ለሕዝብ ብርሃን የሆነ ወንጌል መገለጡን ለማሳየት ነው፡፡ ኢሳ.9፥2

አንድም ጌታ ልደቱ፣ ጥምቀቱ፣ ትንሣኤው እንዲሁም ምጽአቱ በሌሊት ነው፡፡ ይኽም የሆነበት ምክንያት፡- ሌሊቱን ተከትሎ የሚመጣው ብርሃን በመሆኑ ከሞት ወደ ሕይወት ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሲኦል ወደ ገነት የመሸጋገራችን ምሳሌ ነው፡፡

አንድም መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል የሚወርድ ነውና በጌታ ላይ የወረደው ርግብ እንጂ መንፈስ ቅዱስ አይደለም ባሉ ነበር፡፡ በሌሊት ርግብ የለም ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ይታወቅ ዘንድ፡፡

#መንፈስ_ቅዱስ_ለምን_ጌታ_ከውኃ_ከወጣ_በኋላ_ወረደ?
ሀ. ዮሐንስን ያከብሩት ነበርና መንፈስ ቅዱስ የወረደው ለዮሐንስ እንጂ ለጌታ አይደለም ይሉ ነበርና ምክንያቱን ጌታ ውኃ ውስጥ እያለ ከዮሐንስ አልተለየም ነበርና፡፡
ለ. ውኃን የሚባርክ መልአክ እንዳለ ያውቁ ነበርና ውኃውን ለመባረክ አንጂ ለጌታ አይደለም እንዳይባል፡፡
ሐ. ማረፊያ ያጣች ርግብ በባሕር ስትበር አረፈችበት ይሉ ነበርና ሐሳባቸውን በሙሉ ያጠፋ ዘንድ ከውኃ ውስጥ ከወጣ በኋላ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወረደ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

4 months ago

#በጥምቀት_ዙሪያ_የሚነሱ_ጥያቄዎች_እና_መልሶቻቸው
#ጌታችን_ለምን_ተጠመቀ?
1. ምሥጢርን ለመግለጥ፡-
ጌታችን በፈለገ ዮርዳኖስ ሲጠመቅ ምስጢረ ሥላሴ ግልፅ ሆኗል፡፡ አብ በደመና “የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው” በማለቱ አብ የወልድ አባት መሆኑ ታወቀ፡፡ መንፈስ ቅዱስም የባሕርይ ሕይወቱ መሆኑን ሲያስረዳ በአምሳለ ርግብ በራሱ ላይ ተቀመጠ ወልድም በተለየ አካሉ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ ታየ፡፡ ስለዚህ ምሥጢርን ለመግለጥ ስንል የአንድነት የሦስትነት ምስጢር በጐላ ሁኔታ እንዲታወቅ ተጠመቀ ማለት ነው፡፡ /ማቴ. 3፥16/

  1. ትንቢቱን ለመፈፀም፡-
    በመዝሙር 46/47/፥16 ላይ “አቤቱ ውሆች አዩህ፣ ውሆችም አይተውህ ፈሩ ጥልቆች ተነዋወጡ ውሆችም ጮኹ፡፡” ተብሎ በቅዱስ ዳዊት የተነገረውን ትንቢት ለመፈፀም ተጠመቀ፡፡

  2. አርአያ ሊሆነን፡-
    ተጠምቆ እንድንጠመቅ አደረገን ሥርዓትን ሠራልን ቀድሞ በአርአያውና በአምሳሉ እንደፈጠረን አሁንም አርአያ ምሳሌ ሆነን፡፡ ለዚህም ነው ምሳሌን ከእኔ ተማሩ ያለን፡፡ /ማቴ 11፥29/ ለትምህርት ለአርአያ /ዮሐ. 13፥1-17/

  3. የዕዳ ደብዳቤያችንን ለመደምሰስ፡-
    አዳምና ሔዋን ፍዳው በፀናባቸው መከራው በበዛባቸው ጊዜ የሚያቃልልላቸው መስሏቸው ዲያብሎሰ ስመ
    ግብርናችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ ባላቸው ጊዜ አዳም ገብሩ ለዲያቢሎስ (አዳም የዲያብሎስ የወንድ አገልጋይ) ሔዋን ዓመቱ ለዲያብሎስ (ሔዋን የዲያብሎስ ሴት አገልጋይ) ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ዲያብሎስም ይህንን ደብዳቤ አንዱን በሲኦል አንዱን በዮርዳኖስ አስቀመጠው፡፡ በዮርዳኖስ ያስቀመጠውን ጌታችን ሲጠመቅ እንደሰውነቱ ረግጦ ደምስሶታል፡፡ ይህንን ጽሕፈት ለመደምሰስ ነው ጌታችን በዮርዳኖስ የተጠመቀው፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተፃፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፡፡” ያለው ቆላ 2፥14

#ጌታችን_መች_ተጠመቀ?

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀው በ5531 ዓመተ ዓለም ዘመነ ሉቃስ ማክሰኞ ጥር 11 ቀን ከሌሊቱ በ10ኛው ሰዓት ነበር፡፡ ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 19 በተጠመቀም ጊዜ ዕድሜው 30 ዓመት ከ13 ቀን ነበር፡፡ /ሉቃ. 3፥23/

#ጌታችን_ስለምን_በ30_ዓመት_ተጠመቀ?
በብሉይ ኪዳን ሥርዓትና ልማድ ካህናት ለቤተ እግዚአብሔር ተልእኮ እና መንፈሳውያን አገልግሎቶች ከ30 ዓመት ዕድሜ በፊት አደባባይ አይወጡም ነበር፡፡ እጅግ አስፈላጊ እንኳ ቢሆን ከ20 እና 25 ዓመት አስቀድሞ ለአገልግሎት መሰየም ልማድ አልነበረም፡፡ የቤተ እግዚአብሔር አገልጋዮች በዕድሜና በዕውቀት የበሰሉ፣ በጠባይና በሥራ ልምድ የተፈተኑ ተልዕኳቸውን በብቃት ለመወጣት በተገልጋዩ ሕዝብ ዘንድ የተመሰከረላቸው መሆን ነበረባቸው፡፡ /ዘፀ. 4፥3፤1ዜና መዋ. 23፥24፤ 1ጢሞ. 3፥6-10/ ያንን ሥርዓት ለመፈጸም ጌታችን የተጠመቀውና ለትምህርተ ወንጌል የተገለጠው በ30 ዓመቱ ነበር፡፡

ዮሐንስ መጥምቅም የጌታን መምጣት ለማወጅ በዮርዳኖስ ይሁዳ ምድረ በዳዎች ወጥቶ የታየው ከ30 ዓመት ዕድሜው በኋላ ነው፡፡ ሌላው ዐቢይ ምክንያት የሰው ሁሉ መጀመሪያ አዳም የ30 ዓመት ጎልማሳ ሆኖ ተፈጥሮ በ40ኛ ቀን ተሰጥቶት ኋላም በኃጢአት ምክንያት ያስወሰደውን ልጅነት ለማስመለስ ነው፡፡

ክርስቶስ የተጠመቀው ክብር ሽቶ ሳይሆን የአብ የባሕርይ ልጅነቱን (የባሕርይ አምላክነቱን) ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ለማስመስከር፣ ውኃውን ለመቀደስ፣ የአዳምን ልጆች የእዳ ደብዳቤ ለመደምሰስና በስህተት የጠፋውን የልጅነት ክብር ለመመለስ ነው፡፡ ጌታ ተጠምቆ ከውኃው ከወጣ በኋላ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ በማረፍ አብ በደመና ‹‹ይህ ልጄ ነው›› ብሎ ሲመሰክርለት ምሥጢረ ሥላሴ አንድነትና ሦስትነት በጉልህ ተረጋግጧል፡፡ /ማቴ. 3፥16/

#ጌታችን_በዮሐንስ_እጅ_ለምን_ተጠመቀ?

ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ ሲሆን በአገልጋዩ በቅዱስ ዮሐንስ እጅ ይጠመቅ ዘንድ በፍጹም ትሕትና ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ ይህንንም ያደረገልን አብነት ሊሆነን ነው፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ቅዱስ ዮሐንስን ‹‹መጥተህ አጥምቀኝ ›› ብሎት ቢሆን ኖሮ ነገ ነገሥታቱና መኳንንቱ ካህናቱን መጥታችሁ አጥምቁን ባሉ ነበር ስለዚህ እንዲህ እንዳይሆን ነው፡፡ ጌታችን ‹‹ጌታ ስሆን በባርያዬ እጅ እንደተጠመቅሁ እናንተም ወደ ቤተክርስቲያን ሄዳችሁ በካህናት እጅ ተጠመቁ›› ሲል ነው፡፡

ጌታችን በዮርዳኖስ የተጠመቀው ልጅነትን የምታሰጥ ጥምቀትን ባርኮ ቀድሶ ሊሰጠን እንጂ ክብር እንዲሆነው አይደለም፡፡ ምክንያቱም፡- እርሱ እከብር አይል ክቡር እጸድቅ አይል ጻድቅ ነውና፡፡

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ጌታችንን_በማን_ስም_አጠመቀው?

ጌታችን ዮሐንስን አጥምቀኝ ባለው ጊዜ "ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ አንተን በማን ስም ላጥምቅህ? በአብ ስም እንዳላጠምቅህ አብ አባትህ ባንተ ሕልው ነው በወልድ ስም እንዳላጠምቅህ ወልድ አንተ ነህ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንዳላጠምቅህ መንፈስ ቅዱስ ሕይወትህ ባንተ ሕልው ነው ታዲያ በማን ስም ላጥምቅህ?" ብሎ ቢጠይቀው ጌታም ‹‹እንደ መልከጼዴቅ ሥርዓት አንተ የዓለም ካህን ብርሃንን የምትገልጥ የአብ የባሕርይ ልጅ ሆይ ይቅር በለኝ›› ብለህ አጥምቀኝ አለው፡፡

#ዮሐንስ_ጌታን_ሲያጠምቀው_እጁን_ለምን_አልጫነበትም?
- ዮሐንስ በጥምቀት አከበረው /ልዕልና ሰጠው/ እንዳይባል፡፡
- መለኮትን በእጅ መንካት ስለማይቻል

#ጌታችን_ጥምቀቱን_ለምን_በዮርዳኖስ_አደረገው?
በኢየሩሳሌም አካባቢ ብዙ ወንዞች ኩሬዎችና ሐይቆች መኖራቸው የታወቀ ነው፡፡ ጌታ ጥምቀቱን በዮርዳኖስ ያደረገው ስለዚሁ አስቀድሞ የተነገረውን ትንቢት መፈጸሙን ለማረጋገጥ ነው፡፡ ‹‹ባሕር አይታ ሸሸች ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ›› /መዝ.113፥3/ ከዚህም ጋር ከላይ ምንጩ አንድ የሆነው ዮርዳኖስ ዝቅ ብሎ በደሴት ተከፍሎ እንደገና እንደሚገናኝ በግዝረት በቁልፈት (በመገዘርና ባለመገዘር) ተለያይተው የነበሩ ሕዝብና አሕዛብ መላው የአዳም ልጆች በጌታችን ጥምቀት አንድ መሆናቸውን የሚገልጽ ትርጉም አለው፡፡ እስራኤል ዮርዳኖስን ተሻግረው ምደረ ርስት ገብተዋል፡፡ ያመኑ የተጠመቁ ምዕመናንም በጥምቀት ገነት መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉ፡፡ ሌላው በዮርዳኖስ ተጥሎ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤ ይደመስስልን ዘንድ /ቈላ. 2፥14/

#ጌታችን_ለምን_በውሃ_ተጠመቀ?
እግዚአብሔር አምላክ በዘመነ ኦሪት ሰብዐ ትካትን በንፍር ውሃ ፈርኦንና ሰራዊቱን በኤርትራ ባሕር ካጠፋ በኋላ ሰዎች ውሃ ለመዓት እንጂ ለምሕረት አልተፈጠረም ይሉ ነበርና ለምሕረት እንደተፈጠረ ለማጠየቅ በውሃ ተጠመቀ ( ዘፍ 7÷17፤ ዘጸ 14÷1-29)

አንድም ውሃ እሳትን ያጠፋል እናንተም በውሃ ብትጠመቁ ከገሃነመ እሳት ትድናላችሁ ሲል ነው፡፡

አንድም ውሃ መልክን ያሳያል እናንተም በውሃ ብትጠመቁ መልክዓ ሥላሴን የአምላክን ቸርነት ርህራሔ ታያላችሁ ሲል ነው፡፡

አንድም በማር በወተት ቢጠመቅ ኖሮ እነዚህ ለባለጸጎች እንጂ ለድሆች አይገኝም ውሃ ግን በሁሉ ይገኛል፡፡ ስለሆነም ጥምቀት የታዘዘ ለሁሉ ነው ሲል ነው፡፡

አንድም ማርና ወተት ቢታጠብበት ያቆሽሻል እንጂ አያነጣም ውሃ ግን እድፍን ያስለቅቃል እናንተም በማየ ገቦ ብትጠመቁ ከኃጢአት ትጠራላችሁ ሲል ነው፡፡

አንድም ማርና ወተት ተክል ላይ ቢያፈሱት ያደርቃሉ እንጂ አያለመልሙም ውሃ ግን ያለመልማል እናንተም በውሃ ብትጠመቁ ልምላሜ ሥጋ ወነፍስ ታገኛላችሁ ሲል ነው፡፡ (ዮሐ 19÷35)

4 months, 1 week ago

ከጥቂት ወራትም በኋላ ዲዮስቆሮስ ቅስና ሰከላብዮስም ዲቁና ተሾሙ። ዲዮቅልጥያኖስም የክብር ባለቤት ክርስቶስን በካደው ጊዜ ለጣዖታት የማይሰግዱ ክርስቲያኖችን ሁሉ ይገድል ዘንድ የእንዴናው ገዥ አርያኖስን አዘዘው።

አርያኖስም አክሚም ከተማ በደረሰ ጊዜ ኤጲስቆጶሱን አባ ብኑድያስን ያዘውና አሥሮ ወደ አገር ውስጥ ገባ። የእግዚአብሔር መልአክ ሚካኤልም ለዲዮስቆሮስና ለሰከላብዮስ ተገለጸላቸው ወደ መኰንኑም ሒደው የምስክርነት አክሊልን እንዲቀበሉ ነገራቸው እነርሱም ታኅሣሥ ሃያ ስምነት ቀን ሃያ አራት መነኰሳት ሁነው ሔዱ።

ወደ አክሚም ከተማም ሲደርሱ በመድኃኒታችን ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የከበረ የልደትን በዓል ለማክበርና ስለ ከበረ ስሙም ይሞቱ ዘንድ የክርስቲያን ወገኖችን ከሴቶቻቸውና ከልጆቻቸው ጋር ተሰብስበው አገኙአቸው ኤጲስቆጶሱ አባ ብኑድያስም ከእርሳቸው ጋር ገባ። በማግሥቱም አባ ብኑድያስ ቀደሰ አግዮስ ወደሚለው በደረሰ ጊዜ መላእክት እንዲህ ብለው በታላቅ ድምጽ አመሰገኑ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር አሸናፊ ፍጹም የጌትነትህ ምስጋና በሰማይና በምድር የመላ ነው።

ያን ጊዜ መድኃኒታችንን በመሠዊያው ታቦት ላይ ተቀምጦ መላእክትም በዙሪያው ቁመው ቊርባኑን እያነሣ በካህኑ እጅ ላይ በማድረግ የተሰበሰቡትን ሲያቆርባቸው ቅዱሳኑ አዩት።

በዚያንም ጊዜ መኰንኑ አርያኖስ ደረሰ ተቆጥቶም ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ስማቸው ብሕዋፋና ውኒን የሚባሉ ሁለት የሀገር አለቆችን ይዞ ራሳቸውን በሰይፍ ቆረጠ ከእነርሱም በኋላ ዲያቆናትን ንፍቀ ዲያቆናትን መዘምራንን የቤተ ክርስቲያን ሹሞችን ደማቸው ከቤተ ክርስቲያን ደጃፍ ወጥቶ ሃያ ክንድ ያህል እስቲጎርፍ ሴቶችና ልጆችንም ሳያስቀር አረዳቸው።

ከዚህም በኋላ ኤጲስቆጶሱን አባ ብኑድያስን ዲዮስቆሮስን ሰከላብዮስን ከእርሳቸውም ጋር ያሉ መነኰሳትን ከእርሱ ጋር ወሰዳቸው ለጣዖትም ይሰግዱ ዘንድ ሸነገላቸው እምቢ በአሉትም ጊዜ ዐጥንቶቻቸው እስከሚለያዩ ድረስ ይደበድቧቸው ዘንድ አዘዘ የእግዚአብሔርም መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ተገልጾላቸው አዳናቸው የአርያኖስም የጭፍሮቹ ታላላቆች ኮርዮንና ፊልሞና ከጭፍሮችም አርባ ሰዎች ይህን ድንቅ ተአምር አይተው በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ወደ እሳት ማንደጃም እንዲጥሏቸው አዘዘ። ተጋድሏቸውንም ታኅሣሥ ሠላሳ ቀን ፈጸሙ ከተሰበሰቡትም ውስጥ ብዙዎች የሚያሰገድዳቸው ሳይኖር በእውነተኛ አምላክ በክርስቶስ እናምናለን እያሉ ወደ እሳቱ ማንደጃ ራሳቸውን ወረወሩ ምስክርነታቸውንም እንደዚህ ፈጸሙ።

ከዚህም በኋላ ጥር አንድ ቀን ዲዮስቆሮስና ሰከላልብዮስ ታሥረው ሳሉ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ተገለጠላቸውና ምስክርነታቸውን እንዲፈጽሙ አበረታቸው በነጋም ጊዜ ለአማልክት ስለ መስገድ አርያኖስ ተናገራቸው አይሆንም በአሉትም ጊዜ የዲዮስቆሮስን ዐይኖቹን ያወልቁ ዘንድ አዘዘ ቅዱሱም የወለቁ ዐይኖቹን አንሥቶ ወደ ቦታቸው መለሳቸው መኰንኑ ሉክዮስም አይቶ ከሠራዊቱ ጋር በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ ወደ እሳትም ወርውረዋቸው ምስክርነታቸውንም ፈጸሙ።

ከዚህም በኋላ የከበሩ ሰማዕታትን ይገድሏቸው ዘንድ አርያኖስ አዘዘ ሲጸልዩም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠላቸው ስማቸውን ለሚጠራ መታሰቢያቸውንም ለሚያደርግ ገድላቸውንም ለሚጽፍ ከቅዱሳን አንድነት ይቈጥረው ዘንድ ቃል ኪዳን ሰጣቸው። ከዚህም በኋላ ወታደሩ ቀርቦ የቅዱስ ዲዮስቆሮስን ራስ ቆረጠ ሰከላብዮስንም ከወገቡ ላይ ቆረጡት ሃያ አራቱን መነኰሳትም ከቁመታቸው ሠነጠቋቸው በዚች በጥር አንድ ቀን ሁሉም ተቆረጡ ከዘመዶቻቸው የሆነ ሳሙኤልም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም በከበረች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ቀበራቸው በሀገረ አክሚም የተገደሉ ሰማዕታትም ቊጥራቸው ስምንት ሺ አንድ መቶ አርባ ሆነ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥር)

4 months, 1 week ago

#ጥር_1

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጥር አንድ ቀን የዲያቆናት አለቃ የሰማዕታት መጀመሪያ የሆነ የከበረ #ቅዱስ_እስጢፋኖስ ምስክር ሆኖ ሞተ፣ #ቅዱስ_ለውንድዮስ በሰማዕትነት ሞተ፣ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት #አባ_መቃርስ አረፈ፣ #ቅዱሳን_ዲዮስቆሮስ_እና_ሰከላብዮስ (#ቅዱሳን_ሰማዕታተ_አክሚም) በሰማዕትነት አረፉ፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_እስጢፋኖስ_ቀዳሜ_ሰማዕት

በዚህችም ጥር አንድ ቀን የዲያቆናት አለቃ የሰማዕታት መጀመሪያ የሆነ የከበረ እስጢፋኖስ ምስክር ሆኖ ሞተ። ለዚህም ለከበረ እስጢፋኖስ የእግዚአብሔርን ኃይልና ጸጋ የተመላ ሰው እንደነበረና በሕዝቡም መካከል ታላላቅ ተአምራትንና ድንቅ ሥራን ይሠራ እንደነበረ የሐዋርያት ሥራ የተባለ መጽሐፍ ስለርሱ ምስክር ሆነ።

ከዚህም በኋላ አይሁድ ቀኑበት የሐሰት ምስክሮች የሚሆኑ ሰዎችንም አስነሡበት ይህን ሰው በሙሴና በእግዚአብሔር ላይ የስድብ ቃልን ሲናገር ሰምተነዋል እንዲሉ ሐሰትን አስተማሩአቸው። ሕዝቡንና ሽማግሌዎችን ጸሐፊዎችንም አነሣሡአቸው አዳርሱን ብለው ከበው እየጐተቱ ወደ ሸንጎ ወሰዱት።

የሐሰት ምስክሮችንም አቆሙበት እነርሱም ይህ ሰው በቤተ መቅደስ ላይ በኦሪትም ላይ ስድብን ሲናገር ተው ብንለው እምቢ አለ። የናዝሬቱ ኢየሱስ ቤተ መቅደሳችሁን ያፈርሰዋል ሙሴ የሰጣችሁን ኦሪታችሁንም ይሽራል ሲል ሰምተነዋል አሉ።

በአደባባይ ተቀምጠው የነበሩት ሁሉ ተመለከቱት ፊቱንም የእግዚአብሔርን መልአክ ፊት ሁኖ አዩት። ሊቀ ካህናቱም እውነት ነውን እንዲህ አልክ አለው። እርሱም እንዲህ አለ ወንድሞቻችንና አባቶቻችን ስሙ ወደ ካራን ከመምጣቱ አስቀድሞ በሶርያ ወንዞች መካከል ሳለ ለአባታችን ለአብርሃም የክብር ባለቤት እግዚአብሔር ተገለጠለት። ካገርህ ውጣ ከዘመዶችህም ተለይ እኔ ወደማሳይህ ሀገርም ና አለው።

ከዚህም በኋላ ከከላውዴዎን ወጥቶ በካራን ተቀመጠ አባቱም ከሞተ በኋላ ዛሬ እናንተ ወደ አላችሁባት ወደዚች አገር አመጣው። ከዚህም በኋላ የግዝረትን ሥርዓት ሰጠው ይስሐቅንም በወለደው ጊዜ በስምንተኛው ቀን ገዘረው እንዲሁ ይስሐቅም ያዕቆብን ገዘረው ያዕቆብም ዐሥራ ሁለቱን ነገድ አባቶችን ገዘረ።

የቀደሙ አባቶቻችንም በዮሴፍ ላይ ቀንተው ወደ ግብጽ አገር ሸጡት እግዚአብሔር ግን አብሮት ነበር። ከመከራው ሁሉ አዳነው በግብጽ ንጉሥ በፈርዖን ፊትም ዕውቀትን መወደድን ሰጠው በግብጽ አገር ሁሉና በቤቱ ሁሉ ላይ ሾመው። ነገርም በማስረዘም በሰሎሞን እጅ እስከተሠራችው ቤተ መቅደስ ያለውን ተረከላቸው።

ከዚህም በኋላ ድምፁን ከፍ ከፍ አድርጎ እናንተም እንደአባቶቻችሁ ዘወትር መንፈስ ቅዱስን የምታሳዝኑት ዐይነ ልቡናችሁ የታወረ ዕዝነ ልቡናችሁ የደነቈረ አንገተ ደንዳኖች አላቸው። አባቶቻችሁ ከነቢያት ያላሳደዱት ያልገደሉት ማን አለ እናንተ ክዳችሁ የገደላችሁትን የአምላክን መምጣት አስቀድመው የነገሩዋችሁን ገደላችኋቸው።

በመላእክት ሥርዓት ኦሪትን ተቀብላችሁ አልጠበቃችሁም። ይህንንም ሰምተው ተበሳጩ ልባቸውም ተናደደ ተነሣሣ ጥርሳቸውንም አፋጩበት። በእስጢፋኖስም መንፈስ ቅዱስ አደረበት ሰማይም ተከፍቶ ኢየሱስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ የእግዚአብሔርን ክብር አየ። እነሆ ሰማይ ተከፍቶ የሰው ልጅም በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ አያለሁ አለ።

ጆሮአቸውን ይዘው በታላቅ ድምፅ ጮኹ በአንድነትም ከበው ጐተቱት። እየጐተቱም ከከተማ ወደ ውጭ አውጥተው በደንጊያ ወግረው ገደሉት የገደሉትም ሰዎች ልብሳቸውን ሳውል ለሚባል ጐልማሳ ልጅ ያስጠብቁ ነበር። ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ነፍሴን ተቀበል እያለ ሲጸልይ እስጢፋኖስን በደንጊያ ወገሩት።

ዘለፍለፍ ባለ ጊዜም ድምፁን ከፍ አድርጎ አቤቱ ይህን ኃጢአታቸውን ይቅር በላቸው በደልም አታድርግባቸው ይህንንም ብሎ አረፈ። ደጋግ ሰዎችም መጥተው የእስጢፋኖስን ሥጋ ወስደው ቀበሩት ታላቅ ልቅሶም አለቀሱለት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ለውንድዮስ_ሰማዕት

በዚችም ዕለት በከሀዲው መክስምያኖስ ዘመነ መንግሥት ከሶርያ አገር የከበረ ለውንድዮስ በሰማዕትነት ሞተ። የዚህንም ቅዱስ ዜና እግዚአብሔርን የሚያመልክ ተጋዳይ እንደሆነ ንጉሥ መክስምያኖስ በሰማ ጊዜ ልኮ ወደርሱ አስመጣው ሃይማኖቱንም ትቶ አማልክቶቹን ያመልክለት ዘንድ ብዙ ገንዘብ አቀረበለትና ይሸነግለው ጀመረ የከበረ ለውንድዮስ ግን ዘበተበት ስጦታውንም በማቃለል ክብሩን አጐሳቈለ የረከሱ አማልክቶቹንም ረገመ።

ያን ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ በመንኰራኲር ውስጥ ሰቅለው ጽኑዕ የሆነ ሥቃይን እንዲአሠቃዩት አዘዘ። ንጉሥ እንዳዘዘ አደረጉበት የክብር ባለቤት ጌታችን ግን ያለ ጥፋት በጤና አወጣው።

ዳግመኛም በብረት ዘንጎች ይደበድቡት ዘንድ ቅባትና ስብንም በታላቅ ድስት አፍልተው ቅዱስ ለውንድዮስን ከውስጡ ይጨምሩት ዘንድ አዘዘ ይህን ሁሉ ሥቃይንም አሠቃዩት የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያጸናውና ያስታግሠው ያለ ጉዳትም በጤና ያስነሣው ነበር።

ማሠቃየቱንም በደከመው ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ከሥጋውም ድንቆች የሆኑ ብዙዎች ተአምራቶች ተገለጹ ዜናውም በሶርያ አገር ሁሉ ተሰማ አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማት ተሠሩለት ከገዳማቱም በአንዲቱ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት የሆነው የከበረ ሳዊሮስ በሕፃንነቱ ተጠመቀባት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_መቃርስ_ሊቀ_ዻዻሳት

በዚህችም ቀን የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት አባ መቃርስ አረፈ፡፡ እርሱም ለአባቶች ሊቃነጳጳሳት ስልሳ ዘጠነኛ ነው። ከእርሱ በፊት የነበረ አባ ሚካኤልም በአረፈ ጊዜ ኤጲስቆጶሳትና ሊቃውንቱ የግብጽም ታላላቆች ሁሉም ወደ አስቄጥስ ገዳም ወጥተው ለዚች ለከበረች ሹመት ስለሚገባ ከዋሻ ውስጥ ከሚኖሩ ደጋጎች ገዳማውያን ሲጠያየቁና ሲመረምሩ ኖሩ። ከዚህም በኋላ አንድ ጻድቅ ሰው ስለዚህ አባት ነገራቸው እንዲህም አላቸው በአባ መቃርስ ገዳም የሚኖር ቀሲስ አባ መቃርስ እርሱ ለዚች ሹመት ይገባል።

በዚያንም ጊዜ ፈልገው ያዙት እርሱም እኔ ለዚች ሥራ የማልጠቅም በደለኛ ነኝ እያለ ሲጮህ ያለ ፈቃዱ አሥረው ወሰዱት ሊቀ ጵጵስና ሾሙት እንጂ እርሱ የሚላቸውን ቃሉን አልሰሙትም።

ከዚህም በኋላ የሊቀ ጵጵስናውን ሥራ መሥራት ጀመረ በግብጽ አገር በሁሉ ቦታ ኤጲስቆጶሳትን ካህናትን ሾመ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትንም አደሰ ጊዜውም ያለ ኀዘን የጤንነትና የሰላም ጊዜ ነበር። ሹመቱም ሃያ ሰባት ዓመት ከአርባ አንድ ቀን ኖረ እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱሳን_ዲዮስቆሮስ_እና_ሰከላብዮስ (#ቅዱሳን_ሰማዕታተ_አክሚም)

በዚህችም ዕለት የከበሩ የአክሚም ሰማዕታት የምስክርነታቸውን ተጋድሎ ፈጸሙ ዜናቸውም እንዲህ ነው። አክሚም በሚባል አገር ሹም የሆነ አንድ ሰው ነበረ በወርቅ በብር ባለጸጋ ነው ስሙም አልሲድማልዮስ ይባላል ስማቸው ዲዮስቆሮስና ሰከላብዮስ የሚባል ሁለት ልጆችን ወለደ እነርሱም ከመጾምና ከመጸለይ ጋር እግዚአብሔርን በመፍራት አደጉ።

አባታቸውም በሞተ ጊዜ ምንኲስናን ተመኙ የእግዚአብሔርም መልአክ ተገልጦላቸው ወደ ገዳማዊ አባ ሙሴ ገዳም እንዲሔዱ አዘዛቸው ሒደውም በዚያ መነኰሱ ድንቆች ተአምራቶችንም እያደረጉ በብዙ ተጋድሎ ኖሩ።

4 months, 2 weeks ago

"ከእኛ በሚለይበት ልደት እናት የለውም፤ የእኛ በሚመስለው ልደትም አባት የለውም። በፊትም በኋላም የሆነውን ልደቱን ሊናገር የሚችል ማንም የለም።"
ሃይማኖት አበው ዘቅዱስ ኤራቅሊስ

4 months, 2 weeks ago

ትነቅል ዘንድ ሥልጣንን ሰጠህ፡፡ ይህንንም ያደረኩልህ የጳጳሱን ቃል በመናቅ አይደለም፡፡ የፍቅሬን ጽናት ባንተ እገልጽ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ሐዋርያት ወዳልደረሱበት ሕዝብ በመምህርነት እልክህ ዘንድ በሚካኤል ቃል አዲስ ስም አወጣሁልህ፡፡ አንተም በማናቸውም ሥራ ከእነርሱ አታንስም፣ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጌሃለሁና፡፡ ሰውን ሁሉ በእኔ ስም እያስተማርክ ታሳምን ዘንድ፣ ሚካኤልም ባሰብከው ሥራ ሁሉ ረዳት ይሁንህ፣ ሁል ጊዜ ካንተ አይለይም፤ በምትሄድበትም ጎዳና ሁሉ እርሱ መሪ ይሁንህ፤ እኔም ባለ ዘመንህ ሁሉ አልለይህም›› ካላቸው በኋላ ሰላምታ ሰጥቷቸው ዐረገ፡፡

ብፁዕ አባታችንም እጅ ነሥተው ‹‹ለእኔ ለኀጥኡ የማይገባኝ ሲሆን ይህን ሁሉ ጸጋ የጠኸኝ ስምህ በሰማይ በምድር የተመሰገነ ይሁን›› አሉ፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ሀብተ ኃይልን የተመሉ ሆኑ፡፡ ወደቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ሀብት ንብረት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥተው ጨረሱ፡፡ ከዚያም ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ›› ብለው ቤታቸውን እንደተከፈተ ትተው ወንጌልን ለማስተማር ወጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በሀገራችን ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ሕዝቡን ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ኃይማኖት ስለመለሱት በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ተብለዋል፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘተዋሕዶ ፌስቡክ ፔጅ)

We recommend to visit

★ሰውን በማዝናናት የብቃት ማረጋገጫ ያለው ብቸኛው ቻናል ሁሌም Telegram ላይ በጥበብ ደምቀን እናሸበርቃለን

💌 Contact us, @Modenyazbot

»የተመረጡ እና ማንም ያላያቸው የአማሪኛ ቀልዶች እንዲሁም የሚያስደንቁ ስዕሎችንና ቪዲዮ ያገኛሉ።

° ° [ ሙድ እንያዝ በእኛ የአራዶች መዝናኛ ] ° °

° ° Creator @Teke_Man ° °

Last updated 2 weeks ago

☕ ስለ ኢትዮጲያ ቡና የሚወጡ ወቅታዊና ትክክለኛ የክለቡ መረጃዎች አዚህ ያገኛሉ!

➪የዝዉዉር ዜና
☞የአሰልጣኞች አስተያየት
➪ጎሎች እና ቪዲዮዎች
☞የተጨዋቾች የህይወት ታሪክ
➪ጨዋታዎችን በቀጥታ ስርጭት ከየስታድየሙ !

➡መወያያ ግሩፓችን @Ethiopia_coffee_Sc

📩ሀሳብ ወይም አስተያየት ካሎት
በዚህ 👉 @EthiopianCoffeeScBot ✍
BOT ማድረስ ይችላሉ!

Last updated 2 weeks, 1 day ago

እንኳን ወደ # ሉሲ የቴሌግራም ቻናል በደህና መጡ
#የሉሲ /LUCY DINKINESH E/ቤተሰብ ሰለሆኑ ደስብሎናል።

መረጃ መስጠት የምትፈልጉ በዚ አድርሱን 👉 @CACA77

# የኢትዬጵያዊነት የአሸናፊነት መገለጫ አርማችን ነው!
ነፃነታችንን 💪በፈርጣማው ጡንቻችን ይረጋገጣል
👉 ኢትዬጵያዊነት አርበኝነት የማንነት አርማች ነው
🙏🙏🙏

Last updated 1 month, 3 weeks ago